ለዚምባብዌ 2 ቢሊዮን ዶላር ሰብአዊ እርዳታ ያስፈልጋል

በመለሠች ዘለቀ

አለም በበርካታ የተፈጥሮ አደጋዎች እየተፈተነች ትገኛለች፡፡ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ  በአለም አሳሳቢ ደረጃ ላይ ደርሷል። ችግሩ በተለይም  በታዳጊ ሀገራት ላይ የሚያደርሰው ጉዳት ከፍተኛ ነው፡፡ ያደጉ ሀገራት የሚለቁት የካርበን መጠን ለመቀነስ ከነዳጅና ከድንጋይ ከሰል ሀይል ወደ ታዳሽ ለመቀየር ጥረት እየተደረገ ይገኛል፡፡

የአየር ንብረት ለውጥን ለመቀልበስና የአረንጓዴ አሻራ ኢኮኖሚ ለመገንባት የሚደረገውን ጥረት ለማሳካት ያደጉ ሀገራት ድጋፍ ያስፈልጋል፡፡ የችግሩ ሰለባ ከሆኑ የአፍሪካ ሀገራት ዚምባብዌ አንዷ ናት፡፡ የአየር ንብረት ለውጡ በሀገሪቷ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ እያደረሰ ይገኛል፡፡

የዚምባብዌ ፕሬዝዳንት ኢመርሰን ምናንጋግዋ እንዳሉት በሀገሪቷ በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት ድርቅና ረሃብ ተከስቷል። በዚህ ሳቢያ ለሰብአዊ እርዳታ 2 ቢሊዮን ዶላር ያስፈልጋታል ሲሉ ተናግረዋል።

በኤልኒኖ ምክንያት በተከሰተው ድርቅ ሳቢያ ከ80 በመቶ በላይ የሚሆነው የሀገሪቱ ዝናብ ከመደበኛ በታች እንደሆነም ፕሬዝዳንቱ አብራርተዋል።

“የሃገሪቱ ዋና እና ተቀዳሚ ጉዳይ ለሁሉም ዜጋ የእለት ምግብ ተደራሽ ማድረግ ነው።  በተከሰተው ድርቅ ምክንያት አንድም የዚምባብዌ  ዜጋ በረሃብ መሸነፍ ወይም መሞት የለበትም ሲሉም ነው የተናገሩት።

ችግሩን ለመቀልበስና ሰብአዊ እርዳታ ተደራሽ ለማድረግ ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት ኤጀንሲዎች፣ ለሃገር ውስጥ ባለሃብቶች እና የእምነት ድርጅቶች አቤት ብለዋል።

በጎረቤት የዛምቢያ እና የማላዊ መንግስታት ተመሳሳይ እርምጃዎችን ወስደዋል። የፓስፊክ ውቅያኖስን በየሁለት እና ሰባት አመታት የሚያሞቅ በተፈጥሮ የሚከሰት የአየር ንብረት ክስተት /ኤልኒኖ/ በአለም የአየር ሁኔታ ላይ የተለያዩ ተጽእኖዎች አድርሷል። በደቡባዊ አፍሪካ በተለምዶ ከአማካኝ በታች የሆነ የዝናብ መጠን ያስከትላል፡፡ ነገር ግን በዚህ አመት ካለፉት አስር አመታት በላይ የከፋ ድርቅ ታይቷል።

ከ15 ሚሊዮን በላይ የሃገሪቱ ዜጐች ማለትም ከ60 በመቶ በላይ የሚሆነው  የሀገሪቱ ዜጋ ለምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ እና  የልጆች የትምህርት ቤት ወጪዎችን ለመሸፈን በገጠር መሬት በመሸጥ ላይ ይገኛሉ። በጥሬ ገንዘብ ኢኮኖሚ ውስጥ በአንፃራዊነት አነስተኛ ተሳትፎ በመኖሩ፣ ብዙዎቹ በገበያዎች ምግብ የመሸመት አቅማቸው ዝቅተኛ ነው።

የዓለም የምግብ ፕሮግራም ከጥር እስከ መጋቢት ባሉት ወራት  ውስጥ 2 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዚምባብዌያዊያን ማለትም 20 በመቶ የሚጠጋጉ ዜጎች ተጠቃሚ የሚያደርግ የምግብ ዕርዳታ መርሃ ግብር አውጥቷል።

ድርጅቱ በሀገሪቷ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ እንደ ሙቀትና ጎርፍ ባሉ አስከፊ የአየር ሁኔታዎች የተነሳ ረሃብን  ለመከላከል በእርዳታ ኤጀንሲዎች አማካኝነት ድጋፍ እያደረገ ይገኛል።

“ከዘንድሮው የመኸር ወቅት 868 ሺህ ሜትሪክ ቶን እንጠብቃለን:: በመሆኑም ሀገራችን ወደ 680 ሺህ ሜትሪክ ቶን እህል የሚጠጋ የምግብ እህል እጥረት ገጥሞታል:: ይህ ጉድለት ከውጭ በማስመጣት የሚስተካከል ይሆናል” ሲሉ ፕሬዝዳንት ኢመርሰን ምናንጋግዋ ተናግረዋል።

በጎረቤት ዛምቢያ እና ማላዊ ተመሳሳይ እርምጃ ከኤልኒኖ የአየር ሁኔታ ክስተት ጋር ተያይዞ ሰብሎችን አቃጥሎ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች የምግብ ዕርዳታ ፈላጊ መሆናቸው ተመላክቷል።