በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የሂሳብና ሳይንስ እንዲሁም በፈጠራ ስራ ተወዳዳሪና ተፎካካሪ ተማሪዎችን ለማፍራት ጥረት እየተደረገ ነው

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የሂሳብና ሳይንስ እንዲሁም በፈጠራ ስራ ተወዳዳሪና ተፎካካሪ ተማሪዎችን ለማፍራት ጥረት እየተደረገ ነው

ሀዋሳ፡ ጥር 28/2016 ዓ.2016 (ደሬቴድ) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የሂሳብና ሳይንስ እንዲሁም በፈጠራ ስራ ተወዳዳሪና ተፎካካሪ ተማሪዎችን ለማፍራት ጥረት እየተደረገ ይገኛል።

አዲሱ የትምህርት ፖሊሲ በክልሉ ያለልዩነት መጀመሩን የሚያበረታታ ተግባር መሆኑም ተጠቁሟል፡፡

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት የሴቶች ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የ2016 በጀት አመት የአስፈፃሚ አካላትን የ6 ወራት የዕቅድ አፈፃፀም እየገመገመ ይገኛል።

በምክር ቤቱ የማህበራዊ ዘርፍ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወ/ሮ እመቤት ወንድሙ እንዳሉት ኮሚቴው በትምህርት ዘርፍ የነበሩ ጠንካራ ጎኖችን ማስፋትና የታዩ ችግሮች ላይ ምክክር በማድረግ ለቀጣይ የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት ያከናወናል ብለዋል።

የሂሳብና ሳይንስ እንዲሁም በፈጠራ ስራ ተወዳዳሪና ተፎካካሪ ተማሪዎችን ለማፍራት ጥረት ከማድረግ ባሻገር የትምህርት ተደራሽነትና አካታችነት ላይም ሊሰራ ይገባል ሲሉም አክለዋል።

የትምህርት ጥራትን ለማሻሻልና ተደራሽነቱን ለማረጋገጥ፣ መጠነ ማቋረጥና መድገምን እንዲሁም ዜጋን በስነ ምግባር ለማነፅ እየተሰራ የሚገኙትን ተግባራት በ 6 ወራት የዕቅ አፈፃፀም ሪፓርት ተገልጿል።

የተማሪ ቅበላ፣ ትምህርት ጥራት፣ ውስጣዊ ብቃት እንዲሁም ተደራሽነትን ማረጋገጥ ቀሪ ተግባራትን ማከናወን እንደሚያሻም በሪፓርቱ ተመላክቷል።

የአርብቶ አደር አከባቢ ትምህርት ቅበላ፣ የልዩ ፍላጎት ትምህርት፣ ጎልማሶችና መደበኛ ያልሆነ ትምህርት፣ የመምህር ክፍል እንዲሁም መምህር ተማሪ ጥመርታ ላይ የተከናወኑ አበይት ተግባራትና ጉድለቶች በሪፖርቱ ቀርበዋል።

አቶ በላይነህ ባህሩ በቀረበው ሪፖርት ላይ ጥያቄዎችና አስተያየቶች የሰነዘሩ ሲሆን በዚህም በጥንካሬ የታዩ ተግባራትን የማስፋትና በጉድለት የተመዘገቡት አፈፃፀሞች ላይም የእርምት እርምጃ እንዲወሰድባቸው ተጠይቋል።

በተሰነዘሩት አስተያየቶችና ሀሳቦች ዙሪያ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪና ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር አበባዬሁ ታደሰ በትምህርቱ ዘርፍ ለውጥ እንዲመዘገብ ማህበራዊ መሳሪያ የሆነውን ትምህርት ተመጣጣኝ በሆነ መልኩ ማዳረስ ያሻል።

ከትምህርት ቅበላ ጋር በተለይም ልዩ ፍላጎት ላይ የሚታየውን የማህበረሰቡን አመለካከት በመቀየር በአንዳንድ መምህራን በኩል የሚስተዋለውን የክህሎት ችግር ማወቅና መፍታት ያሻል ብለዋል።

የልዩ ፍላጎት ተማሪዎችን መዝግቦ ከማስተማር አንፃር ሰፊ ጉድለቶች ቢኖሩም ማዕከላት ለማደራጀት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ እንደሚገኝም አብራርተዋል።

ቋሚ ኮሚቴው በቀጣይም የሰራተኛና ማህበራዊ፣ ቴክኒክና ሙያ፣ ሴቶችና ህፃናት፣ ወጣቶችና ስፖርት፣ ሳይንስና ቴክኖሎጂ የመንግስት ኮሚዩኒኬሽን እና የጤና ቢሮን የ 6 ወራት ዕቅድ አፈፃፀም ይገመግማል ተብሎ ይጠበቃል።

ዘጋቢ፡ ተመኙህ ገረሱ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን