የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ለመመለስ በቅንጅት ሊሰራ እንደሚገባ የጋሞ ዞን አስተዳደር አስታወቀ

የጋሞ ዞን ምክትል ዋና አስተዳዳሪ አቶ አባይነህ አበራ በጋሞ ዞን ህዝብ ም/ቤት 4ኛ ዙር መርሀ ግብር 10ኛ አመት የስራ ዘመን 19ኛ መደበኛ ጉባኤ ላይ ባደረጉት ንግግር በዞኑ ያለውን አብሮነትና መቻቻል በማጠናከር ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ የሚደረጉ ጥረቶችን አጠናክሮ ማስቀጠል ይገባል ብለዋል።

በሰላምና ጸጥታ፣ ባህላዊ እሴቶችን ማጎልበት ይገባል ያሉት አቶ አባይነህ የዞኑን ሰላም በይበልጥ ለማረጋገጥ ሁሉም አካላት የበኩላቸውን ድርሻ ሊወጡ ይገባልም ብለዋል።

እንደዞን ያለውን ውስን ሀብት በአግባቡ በመጠቀም የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን በተቀናጀ አግባብ መመለስ እንደሚገባ ጠቅሰው እቅድን በተሳካ መልኩ ለመፈፀም በዞኑ ያሉ መዋቅሮች ሀላፊነታቸውን በአግባቡ ሊወጡ እንሚገባም አሳስበዋል።

በጉባኤው አቶ ሰብስቤ ቡናቤ የጋሞ ዞን ብልጽግና ፓርቲ ሀላፊና የመንግስት ዋና ተጠሪ፣ ወ/ሮ ልሳነ ወረቅ ካሳዬ የጋሞ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን መምሪያ ሀላፊ፣ አቶ መኮንን ሞገስ የዞኑ ርእዮተ አለም ዘርፍ ሀላፊና የመንግስት ረዳት ተጠሪ፣ አቶ አብርሀም አርጋው የዞኑ ብልጽግና ፓርቲ የአጀረጃጀት ዘርፍ ሀላፊና የመንግስት ረዳት ተጠሪ ሆነው እንዲሾሙ የቀረበውን ምክር ቤቱ ተቀብሎ አጽድቋል።

ጉባኤው በቀጣይም የጋሞ ዞን አስተዳደር የ2015 በጀት አመት አፈጻጸም ሪፖርትና የ2016 በጀት አመት እቅድ አንዲሁም የዞኑ ረቂቅ በጀት ቀርቦ እንደሚጸድቅ ይጠበቃል።

ዘጋቢ፡ ማርታ ሙሉጌታ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን