የመስዋዕትነት ቀን በጎፋ ዞን ሳውላ ከተማ በተለያዩ ወታደራዊ ዝግጅቶች በድምቀት ተከበረ

የጎፋ ዞን ሰላምና ጸጥታ መምሪያ ኃላፊ ተወካይ ሻለቃ በላይ ብርሃኑ እንደገለፁት የዛሬው ቀን የጀግኖች አርበኞች አባቶቻችንና የአሁኑ ትውልድ ዘመን ተሻጋሪ መስዋዕትነት የሚታወስበት ዕለት ነው፡፡

የሣውላ ከተማ ከንቲባ አቶ ኤርሚያስ ወሰኔ በበኩላቸው የመስዋዕትነት ቀንን ስናከብር ኢትዮጵያ በተሰማራችበት መስክ የድል ባለቤትና በዓለም ደረጃ በጀግንነት የምትታወቅ አገር መሆኗን ለማስታወስ መሆኑን አስረድተዋል።

ለሀገራቸው የተዋደቁ ደማቸውን አፍስሰው አጥንታቸውን ከስክሰው የህይወት መስዋዕትነት በመክፈል ሀገርን ከውጭ ወራሪ የታደጉ የጀግኖች መገኛ አገር መሆኑዋን በመረዳት የምንዘክርበትና መጭው ትውልድ ይህን ታሪክ በመማር የራሱን አሻራ የሚያሳርፍበት ቀን ነው ብለዋል፡፡

የጎፋ ዞን ፖሊስ አዛዥ ኢንስፔክተር ታረቀኝ አጥናፉ የመስዋዕትነት ቀን ሲከበር ለሀገር ስላም ዘብ በመሆንና የተገኘውን ሰላም በዘላቂነት ማሰጠበቅ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡

ያነጋገርናቸው የጸጥታ አካላት ሀገር በዜጎች መሰዋዕትነት በጽናት የምትቆም በመሆኑ አሰፈላጊውን መሰዋዕትነት በመክፈል የሀገርን ጸጥታና ልማት ማረጋገጥ እንደሚገባ አንሰተዋል፡፡

ዘጋቢ፡ ስንታየሁ ሙላቱ – ከሳውላ ጣቢያችን