የጉራጌ ዞን ሳይንስና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ እና የዞኑ ትምህርት መምሪያ በጋራ ያዘጋጁት 5ኛ ዙር የቴክኖሎጂ ፈጠራ ስራዎች ውድድርና ሽልማት አውደ ርዕይ በወልቂጤ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል

የጉራጌ ዞን ሳይንስና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ መምሪያ ኃላፊ አቶ ደምስ ገብሬ አውደ ርዕዩን ባስጀመሩበት ወቅት እንደገለፁት፥ በዞኑ ከ790 በላይ የፈጠራ ስራዎች ውድድር በተማሪዎች፣ በኢንተርፕራይዞች እና በመምህራን እንዲሁም በኮሌጆች እና በግል ተሰርተው ቀርበዋል።

የፈጠራ ስራዎች ምዘናው ሲካሄድ በተገቢው በመከታተልና በአግባቡ በማስመዘን ለውጤት ማብቃት ይጠበቃል ሲሉም አሳስበዋል።

የጉራጌ ዞን ትምህርት መምሪያ ሀላፊ አቶ መብራቴ ወልደማሪያም በበኩላቸው የፈጠራ ስራዎች ውድድሩ በትክክለኛ መንገድ በመመዘን ውጤታማ ተወዳዳሪዎች በክልል መድረክ እንዲሳተፉ እድል የሚፈጥር ነው ሲሉም አስገንዝበዋል።

በዞኑ ካለፉት አራት አመታት ወዲህ በፈጠራ ስራዎች ውድድር አመርቂ ውጤት እየተመዘገበ እንደሆነ ያስታወሱት አቶ መብራቴ አሁንም ወቅቱ የሚፈልግውን የፈጠራ ስራ በመስራት እና በክልል ደረጃ ተፎካካሪ መሆን እንደሚገባም አመላክተዋል።

የፈጠራ ስራዎች ውድድሩ ለሁለት ተከታታይ ቀናት እንደሚቆይም ተመላክቷል።

ዘጋቢ፡ እርካብነሽ ወልደማርቆስ – ከወልቂጤ ጣቢያችን