የአረንጓዴ አሻራ ስራ በአካባቢው ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን በሀዲያ ዞን የሌሞ ወረዳ ደን ልማትና አከባቢ ጥበቃ ጽ/ቤት ገለፀ

የአረንጓዴ አሻራ ስራ በአካባቢው ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን በሀዲያ ዞን የሌሞ ወረዳ ደን ልማትና አከባቢ ጥበቃ ጽ/ቤት ገለፀ

ባለፉት ዓመታት በተከናወነው የአረንጓዴ አሻራ ስራ በአካባቢው ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን በሀዲያ ዞን የሌሞ ወረዳ ደን ልማትና አከባቢ ጥበቃ ጽ/ቤት አስውቋል።

በዘንድሮ ዓመት ከ6 ሚሊየን በላይ ዘርፈ ብዙ ጠቃሜታ ያለቸው ችግኞች ለተከላ መዘጋጀታቸው ተጠቁሟል።

የአረንጓዴ አሻራ ጉዳይ እንደ ሀገርም ትኩረት የተሰጠበት በመሆኑ የሌሞ ወረዳ ተልዕኮውን ለማሳካት ርብርብ እያደረገ መሆኑን የሌሞ ወረዳ ደን ልማትና አከባቢ ጥበቃ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አበራ አሸንቾ ገልጸዋል።

በተያዘው የበልግና የክረምት ወራት ከ6 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ለተከላ መዘጋጀቱን ኃላፊው ጠቁመዋል።

ችግኞቹ በግለሰቦች ማሳ፣ በተቋማትና በመንግሥት ችግኝ ማፍያ ጣቢያች መዘጋጀቱን የጠቆሙት አቶ አበራ፥ ለተከላ የሚሆን 2ሺ 100 ሄክታር መሬት መለየቱንም አስተውቀዋል።

ለአፈርና ውሃ ጥበቃ፣ ለምግብነት፣ ለኢንዱስትሪ፣ ለውበትና ለሌሎች አገልግሎቶችም የሚውሉ የሀገር ውስጥና የውጭ ዝርያ ያለቸው ችግኞች በስፋት መዘጋጀታቸውን ኃላፊው አክለዋል።

በአሁኑ ወቅት የወረዳው የደን ሽፋን 18 በመቶ ማደጉን ያስታወሱት ኃላፊው ይህም ለአከባቢው የአፈር ለምነት መጠበቅ፣ የውሃ ምንጮች ማጎልበት፣ ለምርትና ምርታማነት መጨመር፣ ለዱር እንስሳት መጠለያ፣ ለንብ ማነብ እና ሌሎችም በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የሚመጡ አሉታዊ ተፅዕኖዎችን ለመቋቋም አስተዋጽኦ ከፍ ያለ መሆኑን አስረድተዋል።

የተተከሉ ዛፎችን ከእንስሳትና ከሰዎች ንክኪ ከመታደግ በሻገር በየ መንደሩ የተለያዩ ደንቦችን በመውጣት ከለላ ይደረጋልም ያሉት አቶ አበራ ሁሉም ማህበረሰብ በመጠበቅና በመንከባከብ የድርሻውን እንዲወጣም መልዕክት አስተላልፈዋል።

በወረዳው የአና በሌሣ ቀበሌ አርሶ አደር አቶ ግዛቸው በየነ በማሳቸውን ከ17 ሺህ በላይ ምርጥ ዘር የቡና ችግኞችን በማፍላት ለራሳቸው ከመጠቀም ባለፈ ለአከባቢው ማህበረሰብ ችግኝ እያቀረቡ መሆናቸውን ተናግረዋል።

ዘጋቢ: መንግሥቱ ፊጣሞ – ከሆሳዕና ጣቢያችን