የወረዳውን ዕድገት ለማፋጠን  የተጀመሩ የመሰረተ ልማት ተቋማት ሊፋጠኑ ይገባል

የወረዳውን ዕድገት ለማፋጠን  የተጀመሩ የመሰረተ ልማት ተቋማት ሊፋጠኑ ይገባል

የሣላማጎ ወረዳን ዕድገት ለማፋጠን በሃና ከተማ የተጀመሩ የመሰረተ ልማት ተቋማት ሊፋጠኑ ይገባል ሲሉ የከተማዋ ነዋሪዎች ጠየቁ።

በሐና ከተማ የተጀመረው የመንገድ መሰረተ ልማት ግንባታ የፈጠረው መነቃቃት በሌሎች ዘርፎችችም የሚቀጥል መሆን እንዳለበትም ተመላክቷል።

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በአካባቢው እየተስፋፉ የመጡት የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች አካባቢውን የልማት ኮሪደር እያደረጉት ይገኛሉ።

ያነጋገርናቸው የከተማው ነዋሪዎች  በዕድሜዋ መጠን ባታድግም ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ መነቃቃት ተፈጥሯል ይላሉ።

በተለይ በአራቱም አቅጣጫ እየተገነባ የሚገኘው የአስፋልት መንገድ ግንባታ አካባቢው የኢንቨስትመንት ቀጠና እያደረገው መጥቷልም ባይ ናቸው።

የመንገዱ ግንባታ በከተማው የፈጠረውን መነቃቃት በሌሎች ዘርፎችም ሊቀጥል ይገባል የሚሉት ነዋሪዎቹ በተለይ የንጹህ የመጠጥ ውሃና የኤሌክትሪክ አቅርቦት እንዲፋጠንም ጠይቀዋል።

የከተማው ማዘጋጃ ቤት ስራ አስኪያጅ አቶ ጸጋዬ ደበበ የከተማዋ እድገት አዝጋሚ ሆኖ መቆየቱን በማንሳት ከተማውን አቋርጠው የሚያልፉ መንገዶች በከተማው መነቃቃት መፍጠራቸውን ጠቅሰዋል።

የሰላም እጦት ለእድገት እንቅፋት  በሠላም ግንባታ ላይ ትኩረት ሰጥተው እንደሠሩ የገለጹት ደግሞ የሣላማጎ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ህጉ ቅጣቱ ናቸው።

በዚህ አንድ ወር ጊዜ ውስጥ ብቻም ከ60 በላይ ባለሀብቶች በአካባቢው የኢንቨስትመንት ዘርፍ ለመሰማራት ጥያቄ ማቅረባቸውን ጠቅሰዋል።


ዘጋቢ:- ወንድሜነህ አድማሱ- ከጂንካ ቅርንጫፍ ጣቢያችን