‎‎የሃይማኖት ተቋማት ፅንፈኝነትን፣ አክራርነትንና ከፋፋይ አጀንዳዎችን በመጠየፍ ሰላምና አንድነትን ሊያጠናክሩ እንደሚገባ ተገለጸ

‎‎የሃይማኖት ተቋማት ፅንፈኝነትን፣ አክራርነትንና ከፋፋይ አጀንዳዎችን በመጠየፍ ሰላምና አንድነትን ሊያጠናክሩ እንደሚገባ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ መጋቢት 02/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) የሀይማኖት ተቋማት ፅንፈኝነትን፣ አክራርነትንና ከፋፋይ አጀንዳዎችን በመጠየፍ ሰላምና አንድነትን በማጠናከር የበኩላቸውን እንደሚወጡ የይርጋጨፌ ወረዳ የእምነት ተቋማት ገለፁ።

‎በወረዳው አስተዳደር “የመደመር መንግስት እና የሀይማኖት ተቋማት” በሚል መሪ ቃል ከሀይማኖት መሪዎች ጋር ውይይት ተካሂዷል፡፡

‎የሀይማኖት ተቋማት ማህበረሰቡ በሰላም፣ በፍቅርና በመተሳሰብ ኑሮውን እንዲመራ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን በመድረኩ የይርጋጨፌ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ቡኔ ተናግረዋል፡፡

‎በመሰረተ ልማትና በሌሎች ተግባራት ተቋማቱ ከመንግስት ጎን በመቆም እያደረጉ ያሉትን ድጋፍ አድንቀው፥ ከእምነት አባቶች የሚነሱ ጥያቄዎችን ለመመለስ በቁርጠኝነት እንደሚሠሩ ገልጸዋል፡፡

‎ክርስቲያኑም ሆነ ህዝበ ሙስሊሙ በፆም በሚያሳልፉበት ወቅት ለአገራችን ሠላም ወደ ፈጣሪ በመማፀን የበኩላቸውን እንዲወጡ አስተዳዳሪው ጥሪ አቅርበዋል፡፡

‎የውይይቱ ተሳታፊዎች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ፣ የይርጋጨፌ ወረዳ ኢዲዶ ኢየሱስ ቤተክርስቲያን አገልጋይ ቄሲስ ገደበ ጀቦ፣ የወረዳው ወንጌል አማኞች ካውንስል ሰብሳቢ አቶ ታምራት ገብረማርያምና የእስልምና እምነት ተከታይ አቶ ሁሴን መሐመድ ሁሉም ተከባብሮና ተፈቃቅረው እንዲኖሩ ለምዕመናኑ በየጊዜው ትምህርት እንደሚሰጡ ገልፀዋል፡፡

‎የሀይማኖት ተቋማት ፅንፈኝነትን፣ አክራርነትንና ከፋፋይ አጀንዳዎችን በመጠየፍ ሰላምና አንድነትን በማጠናከር የበኩላቸውን እንደሚወጡ አሳስበዋል፡፡

‎በውይይቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን፣ የካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን የወንጌል አማኞች ካውንስልና የእስልምና እምነት መሪዎች ተሳትፈዋል።

‎ዘጋቢ፦ ውብሸት ኃ/ማርያም – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን