ዘመናዊ የግብርና ግብአት እና ቴክኖሎጂን በተገቢው በመጠቀም የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ እየተሰራ እንደሚገኝ የቀቤና ልዩ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለፀ

ዘመናዊ የግብርና ግብአት እና ቴክኖሎጂን በተገቢው በመጠቀም የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ እየተሰራ እንደሚገኝ የቀቤና ልዩ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለፀ

ጽህፈት ቤቱ ከግብርና ግብአት አቅራቢ ድርጅቶች ጋር በመተባባር በግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ዙሪያ ለአርሶ አደሩ የግንዛቤ ማስጨባጫ መድረክ በወልቂጤ ከተማ አካሂዷል።

የቀቤና ልዩ ወረዳ ግብርና ጽ/ቤት ምክትል ኃላፊና የጽ/ቤት ኃላፊ ተወካይ አቶ ሸምሱ አጃኢብ እንደተናገሩት፤ ልዩ ወረዳዉ ለግብርና ስራዎች ምቹ መሆኑን በመግለፅ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተሰራ እንደሚገኝ ገልፀዋል።

አርሶ አደሩን በዘርፉ ይበልጥ ተጠቃሚ ለማድረግ ግብርና ግብአት አቅርቦት ማዕከል እንዲሁም ከተለያዩ የምርምር ተቋማት ጋር በቅንጅት እየተሰራ ስለመሆኑም ገልፀዋል።

በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የግብርና ተመራማሪ አዲስአለም መብራቱ እንደገለፁት፤ በጥናት የተደገፉ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ስራ ላይ በማዋል የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማረጋገጥ እየተሰራ ይገኛል።

የቀቤና ልዩ ወረዳ በበቆሎ ምርት እና በተለያዩ የግብርና ስራዎች ዉጤታማ እየሆነ መምጣቱን በመጠቆም ይህንን በቴክኖሎጂና በምርምር በመደገፍ ይበልጥ ተጠቃሚ ለማድረግ ይሰራል ብለዋል።

የቀቤና ግብርና ግብአት አገልግሎት ማዕከል ባለቤት አቶ አብድልሰመድ ሀዲ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት፤ ማዕከሉ ከተቋቋመ ጊዜ ጀምሮ ከተለያዩ ድርጅቶች ጋር በመሆን ለአርሶ አደሩ የተለያዩ የግብርና ግብአት ምርቶችን በማቅረብ አርሶ አደሩ ዉጤታማ እንዲሆን እየሰራ ይገኛል ብልዋል።

በተጨማሪም ማዕከሉ ከልዩ ወረዳው ባሻገር በአጎራባች ወረዳዎች ለሚገኙ አርሶ አደሮች የግብርና ምርት እያቀረበ እንደሚገኝ ተናግረው ለዚህም ማዕከሉን ለማስፋፋት እየተሰራ መሆኑን አመላክተዋል።

የመኳንንት እሸቴ አስመጭና ላኪ ድርጅት ተወካይ አቶ ሀይሌ መካ፤ ድርጅቱ በሀገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች በግብርና ስራዎች ላይ ትኩረት አድርጎ እየሰራ እንደሚገኝና በተለይም በልዩ ወረዳው ከቀቤና ግብርና ግብአት አቅርቦት ማእከል እና ከወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመቀናጀት የአካባቢዉን አርሶ አደር ተጠቃሚ በሚያደርጉ ስራዎች ላይ እየሰራ ይገኛል ብለዋል።

በግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኩ ላይ የተገኙ ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት፤ መድረኩ በግብርና ስራዎች ላይ ይበልጥ ዉጤታማ እንዲሆኑ ትምህርት እንዳገኙበት ገልፀዋል። ይህም በዘርፉ ዉጤታማ ለመሆን አስቻይ ሁኔታ እንደሚፈጥርላቸውና ተጠናክረዉ እንደሚሰሩ ተናግረዋል።

ዘጋቢ፡ ሪያድ ሙህዲን – ከወልቂጤ ጣቢያችን