በ6 ወራት ውስጥ ከ12 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ መቻሉ ተገለጸ

በ6 ወራት ውስጥ ከ12 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ መቻሉ ተገለጸ

ሀዋሳ: ጥር 25/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) ባለፉት 6 ወራት በክልሉ ከ12 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ መቻሉን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር) ገለፁ።

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 5ኛ መደበኛ ጉባኤውን እያካሄደ ነው።

የክልሉን ገቢ አሰባሰብ አቅም በማሳደግ በግማሽ ዓመቱ ከመደበኛ ገቢ ብር 10 ቢሊየን 224 ሚሊየን 425ሺህ 237 ወይም የዕቅዱን 106.59% በማሳካት፥ ከማዘጋጃ ቤታዊ ገቢ 2 ቢሊየን 041 ሚሊየን 588ሺህ 193 ወይም የዕቅዱን 92.23% ማሳካት መቻሉ ተመላክቷል፡፡

የታክስ ህግን በማስከበር ረገድ ለግብይት ደረሰኝ ባልሰጡ 195 ግብር ከፋች ሳይ አስተዳደራዊ እርምጃ የተወሰደ ሲሆን በ27 ግብር ከፋዮች ላይ በታክስ ወንጀል ክስ ተመስርቶ በ7 ግብር ከፋዮች ላይ ከሁለት ዓመት እስከ ስድስት ዓመት ከአራት ወራት ጽኑ እስራት እና የገንዘብ ቅጣት ውሳኔ እንዲተላለፍ ተደርጓል፡፡

በአጠቃላይ ብር 12 ቢሊየን 266 ሚሊየን 013ሺህ 430 በመሰብሰብ የክልሉን የልማት አቅም በማሳደግ የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑ ተመላክቷል።

የዚህ ገቢ አፈፃፀም ከ2017 በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር ከጠቅላላ ገቢ የብር 5 ቢሊየን 297 ሚሊየን 150 ሺህ 503 ብልጫ ያለው ነው፡፡

ዘጋቢ፡ ዘላለም ተስፋዬ