የ”ዳራሮ” በዓል ከባህላዊ በዓልነት አልፎ ወደ ቱሪዝም ልማት እንዲቀየር ሰፊ ስራዎች እየተሰሩ ነው – ዝናቡ ወልዴ(ዶ/ር)
ሀዋሳ፡ ጥር 25/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) የ”ዳራሮ” በዓል ከባህላዊ በዓልነት አልፎ ወደ ቱሪዝም ልማት እንዲቀየር ሰፊ ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ(ዶ/ር) ገለጹ፡፡
የጌዴኦ ብሔር ዘመን መለወጫ በዓል “ዳራሮ” በዲላ ከተማ አስተዳደር በድምቀት ተከብሯል።
የ2018 ዓ.ም ዳራሮ በዓል “ዳራሮ ለባህልና ለቱሪዝም ልማት” በሚል መሪ ቃል ነው በከተማ አስተዳደር ደረጃ በሀሮሬሳ ሶንጎ የተከበረው።
የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት ያስተላለፉት የዲላ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ መስፍን ደምሴ(ዶ/ር)፣ የጌዴኦ ባህላዊ የዘመን አቆጣጠርን ተከትሎ የሚከበረው የዳራሮ በዓል እሴቱን፣ ወንድማማችነትንና እህትማማችነትን የሚያስተሳስርና አንድነትን የሚያጎለብት እንደሆነ ገልጸዋል።
በዞን ደረጃ ለሚከበረው የዳራሮ በዓል የዲላ ከተማ እንግዶችን ለመቀበል ዝግጁ መሆኑን ከንቲባው አመላክተዋል።
በበዓሉ አከባበር ላይ የተገኙት የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ(ዶ/ር)፣ የዳራሮ በዓል በዞኑ በሚገኙ በ7 መቶ 25 ሶንጎዎች እየተከበረ መምጣቱን የተናገሩ ሲሆን “ዳራሮ” የሁሉም እንዲሆን እየተሠራ ነው ብለዋል።
ዳራሮ ከባህላዊነት አልፎ ወደ ቱሪዝም ልማት እንዲቀየር ሰፊ ስራዎች እየተሰሩ ነው ያሉት አስተዳዳሪው፤ በዳራሮ በዓል ያሉ እሴቶችን በማስተዋወቅ ለቱሪዝም መደላድል በመፍጠር ኢኮኖሚያዊ ፋይዳውን ከፍ ማድረግ እንደሚያስፈልግ አመላክተዋል።
ጥር 30/2018 ዓ.ም በዲላ ስታዲየም በሚከበረው የዳራሮ በዓል ከ100 ሺህ በላይ ህዝብ ይገኛሉ ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን ሁሉም በበዓሉ እንዲገኝ ጥሪ ቀርቧል።
ዘጋቢ: እስራኤል ቅጣው – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
የህዝቡ የልማትና የመልካም አስተዳዳር ጥያቄዎች በዘላቂነት እንዲመለሱ ከየትኛውም ጊዜ በላይ በልዩ ትኩረት እንደሚሰራ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የኧሌ ዞን ሽግግር ምክር ቤት ገለፀ
መንግስት የደን ጭፍጨፋን በመከላከል የአየር ሚዛንን ለመጠበቅ በሚያደርገው ጥረት ውስጥ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ሚና ከፍተኛ መሆኑን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ደን፣ አካባቢ ጥበቃና የአየር ንብረት ለውጥ ቢሮ እስታውቀ
የህዝቡ የልማትና የመልካም አስተዳደር ችግሮች ለመቅረፍ እንዲያስችል ዞኑ የሚያመነጨውን ገቢ በአግባቡ መሰብሰብ እንደሚገባ የጉራጌ ዞን አስተዳደር አስታወቀ