የአርባምንጭ ማረሚያ ተቋም የህብረ ብሔራዊነት ማሳያ እና የምርታማ ዜጋ ማፍሪያ ተቋም ነው – ኮሚሽነር ብርቱካን መንግስቱ
ሀዋሳ፡ ጥር 18/05/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) የአርባምንጭ ማረሚያ ተቋም የህብረ ብሔራዊነት ማሳያ እና የምርታማ ዜጋ ማፍሪያ ተቋም መሆኑን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ማረሚያ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ብርቱካን መንግስቱ ገለጹ፡፡
በክልሉ ማረሚያ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ብርቱካን መንግስቱ የተመራው ልዑክ በተቋሙ የመስክ ጉብኝት አድርጓል።
ማረሚያ ተቋሙ የ2018 በጀት ዓመት የ6 ወራት የስራ አፈፃፀም ገምግሟል።
የአርባምንጭ ማረሚያ ተቋም ኃላፊ ኮማንደር አለሙ ከኒቶ በእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግራቸው ወቅት፥ ከታድሶ ወዲህ ተቋሙ በሚጨበጡ ለውጦች ውስጥ እንደሚገኝ አብራርተዋል ።
በተቋሙ የታራሚዎች አገልግሎት ምቹና ጤናማ እንዲሆን መደረጉንና በሰብዓዊ መብት አያያዝና በማረምና ማነፅ ስራ የተሻለ አፈፃፀም መመዝገቡን ጠቁመዋል።
ማረሚያ ተቋሙ አነስተኛ መሬትን በመጠቀም በጓሮ አትክልትና ፍራፍሬ ተሰማርቶ ገቢን ለማሳደግ እየተሰራ እንደሚገኝ ያወሱት ኮማንደር አለሙ፥ በቴክኖሎጂ ዘርፍም ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በጋራ በመሰራቱ ለውጥ በማምጣት ላይ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡
የጋሞ ዞን አስተዳደር ተወካይ አቶ ተስፋፅዮን ዘነበ በበኩላቸው፥ ማረሚያ ተቋማት በሪፎርም እሳቤ በመመራት የዘመነ አሰራር ማስፈን እንደሚጠበቅባቸው አሳስበው፥ ታራሚዎችን ማስተማር፣ መምከርና የስራ እድል መፍጠር ይጠበቅባቸዋል ብለዋል፡፡
የታራሚዎችን ሁለንተናዊ ችግር መፍታት የሚያስችል መደላድል ከመፍጠር ባሻገር ሰብዓዊ መብቶቻቸውን ለማክበርና ለማስከበር እየተደረገ የሚገኘው ጥረት የሚበረታታ መሆኑን የገለፁት አቶ ተስፋፅዮን ፥ ተቋሙን ምቹ ለማድረግ ተደጋግፎ መሔድ እንደሚያስፈልግም አሳስበዋል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ማረሚያ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ብርቱካን መንግስቱ፥ የአርባምንጭ ማረሚያ ተቋም የህብረ ብሔራዊነት ማሳያ ከመሆኑ ባሻገር በማረምና ማነፅ ተግባሩም አበረታች እንቅስቃሴ እያደረገ ይገኛል ብለዋል።
በክልሉ ከሚገኙ ማረሚያ ተቋማት ቀዳሚውን የታራሚ ቁጥር ቢይዝም በሙያ ብቁ፣ በስነ-ምግባር የተሻለ፣ በልማት ዘርፍ የተለወጠ ዜጋ እንዲፈራ ባከናወናቸው ተጨባጭ ተግባራት አበረታች ለውጥ ታይቷል ሲሉ አረጋግጠዋል ።
በመርሀ-ግብሩ የተቋሙ የ2018 በጀት ዓመት የ6 ወራት የስራ አፈፃፀም የቀረበ ሲሆን በዚህም ከማረምና ማነፅ ፣ ሰብዓዊ መብትን ከማስጠበቅ ባሻገር በጓሮ አትክልትና ፍራፍሬ ልማት ፣ በአሳ እርባታ በኢትዮ ኮደርስ እንዲሁም በሌሎች የልማት መስኮች የተከናወኑ አበይት ተግባራት በሪፖርቱ ቀርበዋል።
በቀረበው ሪፖርት ዙሪያ የተለያዩ አስተያየቶች እና ጥያቄዎች የተሰነዘሩ ሲሆን ከመድረኩ ምላሽና ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል።
በመጨረሻም ማረሚያ ተቋሙ የተሻለ አፈፃፀም ላስመዘገቡ የተቋሙ ሰራተኞች የማበረታቻ ሽልማት እና ሰርተፊኬት ተበርክቶላቸዋል።
አንዳንድ ተሸላሚዎች የተሰጣቸው እውቅና ለቀጣይ ተግባር የሚያነሳሳ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ዘጋቢ፡ ተመኙ ገረሱ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን

More Stories
በተጀመረው የተፋሰስ ዘመቻ ሥነ ህይወታዊና ሥነ አካላዊ የአፈርና ውሃ ጥበቃን በማጠናከር የአረንጓዴ አሻራችንን ራዕይ መደገፍ እነደሚገባ ተገለጸ
የተፈጥሮ ሀብትን ለመጠበቅና ምርታማነትን ለማረጋገጥ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራን ማጠናከር እንደሚገባ ተገለጸ
በህዝባዊ አንድነት የተጀመሩት የልማት ስራዎች ቀጣይነት እንዲኖረው ሁሉም የበኩሉን ሊወጣ ይገባል