በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የባህልና ቱሪዝም ሀብቶችን በማልማትና በማስተዋወቅ ከዘርፉ የሚጠበቀውን ውጤት ማጎልበት ይገባል – የማህበራዊ ዘርፍ ቋሚ ኮሚቴ

ሀዋሳ፡ ጥር 16/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የባህልና ቱሪዝም ሀብቶችን በማልማትና በማስተዋወቅ ከዘርፉ የሚጠበቀውን ውጤት ማጎልበት እንደሚገባ በክልሉ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የማህበራዊ ዘርፍ ቋሚ ኮሚቴ ገለፀ፡፡

ቋሚ ኮሚቴው የክልሉን ባህልና ቱሪዝም ቢሮ የ2018 በጀት አመት የመጀመሪያ ግማሽ አመት ዕቅድ አፈፃፀምን በወልቂጤ ከተማ ገምግሟል።

በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የማህበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ግዛቸው ዋሌራ እና ሌሎች የቋሚ ኮሚቴው አባላት በተገኙበት የክልሉን ባህልና ቱሪዝም ቢሮ የ2018 በጀት አመት የግማሽ አመት ዕቅድ አፈፃፀም ገምግሟል።

በክልሉ መንግስት የቱሪዝም መዳረሻ ስፍራዎችን በማልማት አዳዲሶችን ጭምር በላቀ የጥራት ደረጃ በመገንባትና በማስተዋወቅ ከዘርፉ የሚጠበቀውን ውጤት ማጎልበት እንደተቻለ ተገልጿል።

በክልሉ የሚገኙ ታሪካዊ ቅርሶችን በማደስ አሻራቸውን በማስቀጠል ለትውልድ እንዲተላለፉ በማድረግና የሀገር ሀብት ምንጭ እንዲሆን ለማድረግ እየተሰራ እንደሚገኝ ተመላክቷል።

ከክልሉ ምክር ቤት የማህበራዊ ዘርፍ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እና አባላት በበጀት አመቱ በዘርፉ የተከናወኑ ጠንካራና መሻሻል በሚገባቸው ተግባራት ላይ ጥያቄና ማብራሪያ የሚሹ አስተያየቶች ተነስተዋል።

በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የማህበራዊ ዘርፍ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ግዛቸው ዋሌራ፤ በክልሉ የሚገኙ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ባህል፣ ቋንቋ እና የቱሪስት መዳረሻ ስፍራዎችን በማልማትና በማስተዋወቅ ከዘርፉ የሚጠበቀውን ውጤት ማጎልበት እንደሚገባ አሳስበዋል።

ለሀገር ልማትና የዕድገት መሰረት ተደርገው ከተያዙት አምስት ዋና ዋና የኢኮኖማ ምሰሶዎች መካከል የቱሪዝም ዘርፉ አንዱ መሆኑን የተናገሩት አቶ ግዛቸው፤ የቱሪዝም መዳረሻ ስፍራዎችን በማልማትና ለዘርፉ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ መሰራት እንዳለበት ገልፀዋል።

ዘጋቢ፡ ቴዎድሮስ ወርቅነህ