የሚድያ አመራሮች ውጤታማ የኮሙኒኬሽንና የህዝብ ግንኙነት ስራዎች በውጤታማነት ለመስራት ሃገራዊ ራዕይን ተከትለው ገዢ ትርክትን ለማስረፅ መስራት እንደሚጠበቅባቸው የጉራጌ ዞን የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች መምሪያ ገለፀ

ይህ የተገለፀው መምሪያው የ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ግማሽ ዓመት የተሰሩ ስራዎች ከወረዳና ከተማ አስተዳደር መዋቅሮችና ባለድርሻ አካላት ጋር ግምገማ ባካሔደበት ወቅት ነው።

የመምሪያው ሀላፊ አቶ ሸምሱ አማን በዚህ ወቅት እንደተናገሩት፤ የሚዲያ አመራሮች ውጤታማ የኮሙኒኬሽንና ህዝብ ግንኙነት ተግባራትን ለማከናወን በትኩረት ሊሰሩ ይገባል።

ገዢ ትርክትን ለማስረፅ አስቻይ ስልቶችን መከተል ተገቢ መሆኑንም አንስተዋል።

በተለይ በቀውስ ጊዜ ዘገባ ወቅት አመራሩ ትክክለኛ መረጃ ለህዝብ ተደራሽ እንዲሆን ለሚዲያ አካላት ወቅታዊ መረጃ በመስጠት ኃላፊነታቸውን መወጣት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል አቶ ሸምሱ።

የመንግስት ሚዲያዎችም ለህዝቡ ተዓማኒና ወቅታዊ መረጃ ለማድረስ መፍጠን እንዳለባቸው አፅንኦት ሰጥተዋል።

በግምገማው ወቅት የተነሱ ጠንካራና ደካማ ጎኖችን በመለየትና የልማት ስራዎችን በማፋጠን ቀጣይ የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ ሚዲያው የራሱን ሚና በትኩረት መወጣት ይገባዋል ሲሉም ተናግረዋል።

ህዝቡ ባለቤት የሌላቸውና ተዓማኒ ያልሆኑ ልማትን የሚያደናቅፉና የህዝቡን አንድነት ከሚሸረሽሩ መረጃዎች በመቆጠብ የበኩሉን ሚና መጫወት እንዳለበትም አቶ ሸምሱ አመላክተዋል።

ከመድረኩ ተሳታፊዎች መካከል አቶ ፀጋዬ ገብሬ እና አቶ እስክንድር እንድሪያስ በሰጡት አስተያየት፤ ከመድረኩ ጥሩ ልምድ መቅሰማቸውን ጠቅሰው በተለይ በጉራጊኛ ቋንቋ መረጃ ከማሠባሠብና ከማሰራጨት ጋር የተስተዋሉ ክፍተቶችን ለማረም በትኩረት እንደሚሰሩ ገልፀዋል።

በተቋም ደረጃ የተሰሩ ስራዎችን በምርጥ ተሞክሮነት ቀምሮ ለሌሎች ከማስተማር አንፃርም በቀጣይ ይበልጥ እንደሚሰሩ ተናግረዋል።

ዘጋቢ፡ እቴነሽ ቲሬቦ – ከወልቂጤ ጣቢያችን