በደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግሥት ዲላ ክላስተር እየተገነባ ላለው የክልል ቢሮዎች ህንጻ ግንባታ የመሠረት ድንጋይ የማስቀመጥ መርሃግብር ተካሄደ

መርሃግብሩን ያስጀሩት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግሥት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የዲላ ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃለፊ ዶክተር መሪሁን ፍቅሩ፤ መንግሥት ጀምሮ በመጨረስ መርህ በክልሉ ካሉት ስድስት ማዕከል አንዱ በሆነው በዲላ ክላስተር የሚገነባው የክልል ተቋማት ህንጻ በቅርብ ጊዜ ቢጀመርም ሥራዉ በፍጥነት እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቅሰዉ በግንባታው እየተሳተፉ ያሉትን አካላት ሁሉ አመሰግነዋለሁ።

ግንባታዉ በአጭር ጊዜ ተጠናቆ ወደ ሥራ ለመግባት ትኩረት ሰጥተዉ እየሰሩ እንደሚገኙ የተናገሩት ኃላፊው ለዚህ አላማ ስኬት ሁሉም የድርሻዉን እንዲወጣ አሳስበዋል።

እንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ያደረጉት የዲላ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ዶክተር መስፍን ደምሴ፤ መንግሥት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መንግሥት በህዝብ ፍላጎት መነሻ እንዲደራጅ ካደረገ ወዲህ በርካታ የልማትና የመልካም አስተዳር ጥያቄ እየመለሰ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

መንግሥት ዜጎች የሚያነሱትን ፍትሃዊ አገልግሎት ጥያቄ ለመመለስና አገልግሉቱን በሁሉም አካባቢ ተደራሽ ለማድረግም ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ነው።

የጌዴኦ ዞን አስተዳዳሪ ዶክተር ዝናቡ ወልዴ፤ ክልሉ ከተደራጀ ወዲህ ከተሞች እኩል እንዲያድጉ ያለዉን ቁርጠኝነት እያዩ እንደሚገኙ ጠቅሰዉ ግንባታው እስከሚጠናቀቅ ዞኑ የሚጠበቅበትን ሁሉ ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን ገልጸዋል።

ለህንጻዉ ግንባታ ከ4 መቶ ሚሊየን ብር በላይ ወጪ እንደሚደረግ የተገለጸ ሲሆን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግሥት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የዲላ ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ ዶክተር መሪሁን ፍቅሩ፣ ሌሎች የክልል፣ የዞንና ወረዳ አመራሮች በተገኙበት የመሠረት ድጋይ ተቀምጧል።

ዘጋቢ: አማኑኤል ትዕግስቱ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን