በአገር አቀፍ ደረጃ ለሚካሄደው የምዕራፍ-2 የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ በአርባምንጭ ስልጠና መሰጠት ተጀመረ
ስልጠናውን በክልሉ ከሚገኙ 8 ዞኖች የተውጣጡ ከ1 ሺህ 100 በላይ ሰልጣኞች ለ10 ተከታታይ ቀናት እንደሚወስዱም ተጠቁሟል።
ሀገራችን ኢትዮጵያ ፈጣንና ቀጣይነት ያለው ሁለንተናዊ ለውጦችን ለማስመዝገብ የሚያግዝ እና ፍትሐዊ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጥ ሀገራዊ የልማት አጀንዳን ቀርፃ እየተንቀሳቀሰች እንደምትገኝ ይታወቃል።
ከዚሁ አገራዊ አጀንዳ ጋር የሚናበብ እቅድ ተዘጋጅቶ ከዳር ለማድረስ ከፍተኛ ርብርብ እየተደረገ ሲሆን የኢትዮጵያ ስታትስቲክስ አገልግሎትም ያላሳለሰ ጥረት እያደረገ ይገኛል።
በኢትዮጵያ ስታትስቲክስ አገልግሎት የአርባምንጭ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ስሜ አንበሴ፤ አገልግሎቱ ሀገራዊ የልማት አጀንዳዎችን ለማሳካት ተጨባጭና ወቅታዊ መረጃዎችን በመሰብብ ለሚመለከተው አካል ሲያደርስ መቆየቱን አብራርተዋል።
ሁሉም ሰልጣኝ በትጋት እና በጥራት መረጃዎችን መሰብሰብ ይጠበቅብናል ያሉት አቶ ስሜ፤ የገጠር ትራንስፎርሜሽን፣ የዲጂታል ኢኮኖሚን በሚያሳልጡ ተግባራት ላይ ትኩረት ከማድረግ ባሻገር የመረጃን ሚስጥራዊነትን በመጠበቅ የሀገራችንን የለውጥ ግስጋሴ መደገፍ ያስፈልጋል ብለዋል።
የጋሞ ዞን አስተዳደር ልዩ አማካሪ እና የአስዳዳሪው ተወካይ አቶ ተስፋፂዮን ዘነበ በበኩላቸው፤ ለሀገራችን ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና መሰረተ ልማት እድገት እውነተኛና ተአማኒነት ያለው መረጃ መሰብሰብ ወሳኝነት አለው ሲሉ አሳስበዋል።
መረጃው ለሀገራችን ብሎም ለዞናችን እድገት ወሳኝ በመሆኑ አሰልጣኞች በስልጠናው ወቅትም ሆነ ከስልጠናው በኋላ በጥብቅ ዲሲፕሊን መመራት እንዳለባቸው አሳስበዋል።
የአርባምንጭ ከተማ ንግድና ኢንዱስትሪ መምሪያ ኃላፊና የከንቲባው ተወካይ አቶ መኮንን ጋትሶ፤ ቁልፍ የሆነውን ሀገራዊ ተልዕኮን ለማሳካት መረጃን በትክክል በመሰብሰብ ሀገራዊ ሀላፊነታችሁን ልትወጡ ይገባል ብለዋል።
በአርባምንጭ ዩኒቨርስቲ የውሀና ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ዳይሬክተር ዶ/ር ታምሩ ተሰማ እንደተናገሩት፤ መረጃ መሰብሰብ ታላቅ ሀገራዊ አደራ በመሆኑ ለሀገራችን የኢኮኖሚ አቅም ከፍተኛ አስተዋፅኦ ስለሚኖረው በእውቀትና በመረጃ ስራውን መስራት ያስፈልጋል፡፡
በቆጠራው በከተማና ገጠር ሁሉንም የኢኮኖሚ ድርጅቶች የሚያካትት ሲሆን በተለይም ማምረቻ፣ ግንባታ፣ ማዕድን፣ ንግድ አገልግሎት ዘርፎች፣ መደበኛና ኢ-መደበኛ፣ ጥቃቅንና አነስተኛ እንዲሁም መካከለኛና ትላልቅ ድርጅቶች እንደሚካተቱ ጠቁመዋል።
በስልጠናው በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከሚገኙ 8 ዞኖች የተውጣጡ ከ1 ሺህ 100 በላይ ሰልጣኞች ለ10 ተከታታይ ቀናት እንደሚሳተፉ ለማወቅ ተችሏል።
ዘጋቢ፡ ተመኙህ ገረሱ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን
በአገር አቀፍ ደረጃ ለሚካሄደው የምዕራፍ-2 የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ በአርባምንጭ ስልጠና መሰጠት ተጀመረ

More Stories
ኢትዮጵያ እያስመዘገበች ያለው ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ቀጣይነት እንዲኖረው የአምራች ድርጅቶች ቆጠረ እና ምዝገባ ጉልህ ሚና እንደሚኖር በኢትዮጵያ ስታትስቲክስ አገልግሎት የሆሳዕና ቅርንጫፍ አስታወቀ
የፍትህ ዘርፍ ባለሙያዎችን አቅም ማጎልበት በፍትህ ስርዓት ላይ የሚነሱ ችግሮችን እንደሚቀርፍ ተጠቆመ
በስራ ቦታቸው ላይ የህፃናት ማቆያ ማዕከል መቋቋሙ ስራቸውን በአግባቡ ለማከናወን እንዳስቻላቸው የማእከሉ ተጠቃሚ እናቶች ገለፁ