20ኛው የብሔር ብሔረሰቦች ቀን በስኬት እንዲከበር ሚዲያዎች የነበራቸው ሚና ከፍ ያለ እንደነበር የፌደሬሽን ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር ተናገሩ

የበአሉን አከባበር የማጠቃለያ ግምገማና ለሚዲያዎች የዕውቅና መርሀ ግብር በአዲስ አበባ ከተማ ተከናውኗል።

በዚህ ወቅት ንግግር ያደረጉት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፤ በዘንድሮው የብሔር ብሔረሰቦች በዓል የመገናኛ ብዙሀን ዘጋቢ ፊልሞችን በማዘጋጀት የቀጥታ ስርጭት በመስራትና ልዩ ልዩ ዘገባዎችን ለህዝቡ በማድረስ ሚናቸውን ተወጥተዋል ብለዋል።

በተለይ ከለውጡ ማግስት የተከበሩ ሁሉም በዓላት ህብረ ብሄራዊ አንድነትን በማጠናከር ከፍ ያለ ሚና ተጫውተዋል ነው ያሉት።

የለውጡ ፍሬ በሆነው የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በዓሉ መከበሩም የዚሁ ማሳያ ስለመሆኑ አመላክተዋል።

በዓሉ ክብሩን ጠብቆና ህብረ ብሔራዊነትን በሚያሳይ መልኩ እንዲከበር አዲሱ ክልል የሰራው ተግባር ከመቼውም በላይ የሚደነቅ መሆኑን አፈ ጉባኤው አመላክተዋል።

በዓሉ አላማውን ያሳካ እንዲሆን የበኩላቸውን ለተወጡ ምስጋና ያቀረቡት አቶ አገኘሁ፤ ለሚዲያ አካላትም ምስጋናና ዕውቅና ሰጥተዋል።

ዘጋቢ፡ ባዬ በልስቲ