“ከጂኦ ስትራቴጂካዊ ኩስምና ወደ ታደሰ ቁመና” በሚል መሪ ቃል የካፋ ዞን ፖሊስ መምሪያ አመራር አባላት የስልጠና መድረክ ተጀመረ

“ከጂኦ ስትራቴጂካዊ ኩስምና ወደ ታደሰ ቁመና” በሚል መሪ ቃል የካፋ ዞን ፖሊስ መምሪያ አመራር አባላት የስልጠና መድረክ ተጀመረ

ስልጠናውን በንግግር የከፈቱት የዞኑ ፖሊስ አዛዥ ኢንስፔክተር ዳዊት ደሳለኝ በሁሉም መዋቅሮች ስልጠናው እየተሰጠ ይገኛል ብለዋል።

በቀጣይ ለሚኖሩ ሀገራዊ ተልዕኮዎች ዝግጁ ለመሆን እንዲሁም ከውስጥና ከውጭ የሚቃጡ ችግሮችን ለመግታት የሚያግዝ በመሆኑ ሰልጣኞች በአግባቡ መከታተል እንዳለባቸው አሳስበዋል።

የዞኑ ሠላም፣ ጸጥታና ሚሊሻ መምሪያ ኃላፊ አቶ ክፍሌ ጋነቾ፤ የፖሊስ ሠራዊቱ በተሰማራበት የሥራ መስክ በታማኝነት፣ በልበ-ሙሉነትና በታታሪነት ተግባሩን እንዲመራ ታስቦ የተዘጋጀ ስልጠና ነው ብለዋል።

የፖሊስ ሠራዊት አባላት ለሀገር ዕድገትና ሉዓላዊነት መከበር የድርሻቸውን ሊወጡ እንደሚገባ አሳስበዋል።

የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማሳጣት የሚደረጉ ጥረቶችን መመከት እንደሚያስፈልግ ነው የተናገሩት።

የካፋ ዞን ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ ወይዘሮ አሚና ሀሰን ወቅቱ ሀገራችን ከተረጂነት ለመላቀቅ እየተጋች ያለችበት ወቅት በመሆኑ የስልጠናው ፋይዳ የጎላ ነው ብለዋል።

ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም መከበር የፖሊስ አባላቱ የበኩሉን ጥረት እንዲያደርግ አሳስበዋል።

ስልጠናው በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ፖሊስ ኮሚሽን የወንጀል መረጃ ኢንተለጀንስ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር በሆኑት ረዳት ኮሚሽነር በላይነህ በቀለ እየተሰጠ ነው።

ዘጋቢ፡ ሀብታሙ ገብሬ – ከቦንጋ ጣቢያችን