ከተማ አስተዳደሩ በጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዝ ለተደራጁ ወጣቶች የማምረቻ ሼድ ርክክብ አደረገ

ከተማ አስተዳደሩ በጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዝ ለተደራጁ ወጣቶች የማምረቻ ሼድ ርክክብ አደረገ

‎የዲላ ከተማ አስተዳደር ሥራና ክህሎት መምሪያ በጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዝ ለተደራጁ ሥራ ፈላጊ ወጣቶች ያዘጋጀውን ማምረቻ ሼድ ርክክብ አድርጓል፡፡

‎በርክክብ ስነ-ስርዓቱ የዲላ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የሥራና ክህሎት መምሪያ ኃላፊ አቶ ታሪኩ በየነ፤ ማምረቻ ሼዱ የተበረከተላቸው VIS ከተሰኘው ግብረሰናይ ድርጅት የክህሎት ስልጠና የወሰዱና 4 ነጥብ 5 ሚሊዮን የሚገመት መሥሪያ ቁሳቁስ ድጋፍ የተደረገላቸው ወጣቶች መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡

‎በ10 ማህበራት የተደራጁ 56 የሚሆኑ ወጣቶች በICT፣ በእንጨት ሥራ፣ በጨርቃጨርቅ፣ በቆዳና የቆዳ ውጤቶች እንዲሁም በሌሎች ዘርፎች የክህሎት ስልጠና ሲከታተሉ የቆዩ መሆናቸውን ምክትል ከንቲባው አስረድተዋል፡፡

‎የዲላ ከተማ አስተዳደር ብልጽግና ፓርቲ ኃላፊና የመንግሥት ዋና ተጠሪ አቶ መንግስቱ ተክሌ በበከኩላቸው፤ መንግሥት ለሥራ አጥ ወጣቶች ጥያቄ ተግባራዊ ምላሽ እየሰጠ መሆኑን ገልጸው እንደ ዲላ ከተማም በርካታ ወጣቶችን በጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች በማደራጀት ወደ ሥራ የማስገባቱ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

‎በቀጣይም የወጣቱን ተጠቃሚነት በዘላቂነት ለማረጋገጥ በሀገር ውስጥና የውጪ ሀገር የሥራ አማራጮች ወጣቱን በማሳተፍ ከራሳቸው አልፈው ለሀገር አምራች ዜጎች እንዲሆኑ በትኩረት እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

‎የተፈጠረላቸው ምቹ ዕድል የሴቶችንና አካል ጉዳተኞችን እኩል ተጠቃሚነት ያረጋገጠ በመሆኑ መደሰታቸውን የጠቆሙት የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ወጣቶቹ፤ በቀጣይ በሚሠማሩበት ዘርፍ ውጤታማ በመሆን ለሌሎች ወጣቶች አርአያ ለመሆን ጠንክረው እንደሚሠሩ ተናግረዋል፡፡

‎ዘጋቢ፡ ሳሙኤል በቀለ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን