ከ2 ሺህ በላይ አዲስ ሰልጣኞችን ተቀብሎ ለማሰልጠን መታቀዱን የሆሳዕና ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ አስታወቃ
ሀዋሳ፡ ጥቅምት 25/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) በ2018 የስልጠና ዘመን እንደ ሀገር የአከባቢን ፀጋ ታሳቢ በማድረግ ከ2 ሺህ በላይ አዲስ ሰልጣኞችን ተቀብሎ ለማሰልጠን መታቀዱን የሆሳዕና ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ አስታወቃ።
ከመደበኛ ስልጠና ጎን ለጎን ከ20 ሺህ በላይ የአጫጭር ጊዜ ሰልጣኞችን ተቀብሎ በማሰልጠን ለሀገር ውስጥና ለውጭ ሀገራት የስራ ስምሪት የማብቃት ስራ እንደሚሰራ ተመላክቷል።
በኮሌጁ የ2018 የስልጠና ዘመን ስራ ከመጀመሩ አስቀድሞ የመማሪያ ክፍሎች፣ የስልጠና ወርክሾፖችና የግብአት አቅርቦት ስራዎች እንዲሟሉ በማድረግ ከ2 ሺህ በላይ ነበር ሰልጣኞችን በመቀበል ስልጠና መጀመሩን የኮሌጁ ዲን አቶ አወል ሸንጎ ተናግረዋል።
በአሁኑ ወቅት ከ2 ሺህ እስከ 3 ሺህ የሚደርሱ አዲስ ሰልጣኞችን እንደ ሀገር የአካባቢዎቹን ፀጋ ከግምት በማስገባት በኮንስትራክሽን፣ በግብርና፣ በውሃ ዘርፍና በሌሎችም የስልጠና መስኮች ተቀብሎ ለማሰልጠን በቴክኖሎጂ የታገዘ የOnline ምዝገባ እየተካሄደ መሆኑን ገልጸዋል።
ከዚህ ቀደም ከኮሌጁ በተለያዩ የሙያ መስኮች ሰልጥነው የወጡ ሰልጣኞች በግልም ሆነ በማህበር ተደራጅተው በመስራት ውጤታማ መሆናቸውን የተናገሩት አቶ አወል፥ በተለይ የዘንድሮ አዲስ ተመዝጋቢ ሰልጠኞች እንደ አከባቢው በተለዩ የስልጠና ዘርፎች ይበልጥ ውጤታማ መሆን እንደሚችሉ አስረድተዋል።
ኮሌጁ ለአካል ጉዳተኛ ሰልጣኞች ከክፍያ ነፃ አገልግሎት የሚሰጥ መሆኑንም አቶ አወል አስታውቀዋል።
ኮሌጁ ከመደበኛ ስልጠና ጎን ለጎን ለሀገር ውስጥና ለውጭ ሀገራት የስራ ስምሪት በተለያዩ ዘርፎች የአጫጭር ጊዜ ስልጠናዎችን እንደሚሰጥ የተናገሩት ዲኑ፥ ባለፈው አመት 13 ሺህ ሴቶች ወደ ውጭ ሀገራት ለስራ ስምሪት ከመሄዳቸው አስቀድመው ስልጠና እንዲያገኙ መደረጉን ጠቁመው ዘንድሮም ከ20 ሺህ በላይ ሰልጣኞችን ለማሰልጠን መታቀዱን ገልጸዋል።
ከኮሌጁ አሳልጣኞች መካከል ብሩክ አምባውና ረድኤት ፈለቀ በበኩላቸው ወደ ኮሌጁ የሚመጡ ሰልጣኞች በቂ እውቀት አግኝተው እንዲወጡ ለማድረግ የበኩላቸውን እየተወጡ መሆናቸውን ተናግረዋል ።
በኮሌጁ የ3ኛ አመት የፋሽን ዲዛይን ሰልጣኝ የሆነችው ፍሬሕይወት በቀለ እና የአይሲቲ የ3ኛ ዓመት ሰልጣኝና አካል ጉዳተኛ የሆነችዉ ፀሐይ ወልዴ በሰጡት አስተያየት በኮሌጅ በሚገኙ ወርክሾፖች የተደራጀ የስልጠና ግብአት ተሟልቶላቸው በቂ እውቀት እያገኙ ስለመሆናቸው ገልጸዋል።
ኮሌጁን ለመጀመሪያ ጊዜ ከተቀላቀሉ አዲስ ሰልጣኞች መካከል ብሌን አዲሴና መብራቴ ደጉ እንዳሉት በኮሌጁ በተደረገላቸው አቀባበል ደስተኛ መሆናቸውን ጠቅሰው በቀጣይ በመረጡት ዘርፍ ተገቢውን ሙያ ቀስመዉ በመውጣት ራሳቸውንም ሆነ ሀገራቸውን ለመጥቀም ጠንክረው እንደሚሰሩ ተናግረዋል።
ዘጋቢ : ተሻለ ከበደ – ከሆሳዕና ጣቢያችን

                
                                        
                                        
                                        
                                        
More Stories
እየተከናወነ ያለውን የኮሪደር ልማት ሥራ ከዳር ለማድረስ በሚደረገው ርብርብ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሙዱላ ከተማ አስተዳደር ገለፀ
በትምህርት ሴክተር የመረጃ አያያዝ ውጤታማነት ዙሪያ በኩረት እየተሠራ መሆኑ ተገለጸ
ሁሉንም የመማሪያ መጻሕፍት ባለማግኘታቸው በትምህርታቸው ላይ ጫና እየፈጠረባቸው መሆኑን በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ወረዳ የቆንጋና ቆቄ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች ተናገሩ