ፓርቲው በየወቅቱ የሚያዘጋጃቸው የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች የአባሉን የመፈፀም አቅም እያጎለበቱ እንደሚገኙ ተገለጸ

‎የብልጽግና ፓርቲ በየወቅቱ ለአባላቱ የሚያዘጋጃቸው የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች የመፈፀም አቅማቸውን እያጎለበተ መሆኑን የይርጋጨፌ ከተማ አስተዳደር አባል አመራሮች ተናገሩ።

‎በጌዴኦ ዞን የይርጋጨፌ ከተማ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት በተሻሻሉ መመሪያዎች ዙሪያ የአሰልጣኞች ስልጠና ሰጥቷል።

‎በስልጠናው መክፈቻ የይርጋጨፌ ከተማ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ መብራቱ ኦብሰ፤ የብልጽግና ፓርቲ ውስጣዊ እና ዉጫዊ ፈተናዎችን ተቋቁሞ በርካታ ድሎችን እያስመዘገበ እንደሚገኝና ድሉን ለማስቀጠል የአባሉን አቅም የሚያጎለብቱና ውስጣዊ አንድነትን የሚያጠናክሩ መሰል ስልጠናዎች ፋይዳቸው የጎላ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

‎ስልጠናው ቀጣይነት ያለውና ሁሉም አባል ሀገሪቱ ያለችበትን አሁናዊ ነባራዊ ሁኔታን በመገንዘብ እንደሀገር ለተያዙ ግዙፍ እቅዶች ስኬት የበኩሉን እንዲወጣ ከመርዳቱም ባሻገር፤ የፓርቲውን የአሠራር ሥርዓት ጠንቅቆ በማወቅ የጋራ ትርክትን መገንባት በሚያስችሉ እሳቤዎች ላይ አበክሮ ለመሥራት አጋዥ ኃይል መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

‎በስልጠናው የተሳተፉ የፓርቲው አባላት፤ ፓርቲው ዓለም አቀፋዊ እውነታዎችን በመገንዘብ የኢትዮጵያን የተደማጭነት አቅም ከፍ ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት እያደረገ መሆኑን እና መሰል ስልጠናዎች ስለፓርቲው የአሠራር ደንብና መመሪያዎች ያላቸውን ግንዛቤ ከፍ ያደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

‎ያገኙትን ስልጠና ወደ ውጤት ለመቀየር ተግተው እንደሚሠሩ የጠቆሙት የስልጠናው ተሳታፊዎች፤ በቀጣይ ያገኙትን ግንዛቤ ለተቀሩት አባላት የማስረጽ ኃላፊነታቸውን በአግባቡ እንደሚወጡ አስታውቀዋል፡፡

‎ዘጋቢ: ሳሙኤል በቀለ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን