በህገ-ወጥ የንግድ ስራዎች የሚንቀሳቀሱ አንዳንድ ግለሰቦች እና ድርጅቶች በህጋዊ መንገድ የሚሰሩ ነጋዴዎች ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ እያሳደሩ መሆኑን አንዳንድ የአርባምንጭ ከተማ ነጋዴዎች ገለፁ

‎የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ በህገ-ወጥ መንገድ ሲንቀሳቀሱ በነበሩ ከ8 ሺህ 4 መቶ በላይ ድርጅቶችና ግለሰቦች ላይ እርምጃ መውሰዱን አስታዉቋል።

‎አንዳንድ የአርባምንጭ ከተማ ነጋዴዎች፤ በህጋዊ መንገድ በተለያዩ የንግድ ስራዎች ላይ ተሰማርተው እየሰሩ መሆናቸውን ጠቁመው ህጋዊነትን በመጣስ የሚሰሩ አንዳንድ ነጋዴዎች በሀገርና በህዝብ ላይ የሚያሳድሩት አሉታዊ ተጽዕኖዎች ከፍ ያለ እንደሆነ ተናግረዋል።

‎የሚስተዋለውን ህገወጥ ተግባር ለመከላከል በርካታ የቁጥጥር እና የክትትል ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ሰናይት ሰለሞን ተናግረዋል።

‎ህጋዊ የንግድ ስርዓትን በመጣስ በህገ-ወጥ መንገድ ሲንቀሳቀሱ በነበሩት ግለሰቦችና የንግድ ድርጅቶች ላይ ህጋዊ እርምጃዎች እንደተወሰዱ መሆኑን ኃላፊዋ ገልፀዋል።

‎በተያዘው በጀት ዓመት የምርት አቅርቦት በማሳደግና የሰንበት ገበያዎችን በተጨማሪ በማቋቋም ለህብረተሰቡ መሰረታዊ የፍጆታ ዕቃዎችንና የግብርና ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ የሚስተዋለውን የኑሮ ዉድነት ለማረጋጋት በከፍተኛ ቁርጠኝነት እየተሰራ መሆኑን ወ/ሮ ሰናይት ሰለሞን ጠቁመዋል።

‎ዘጋቢ፡ ስምረት አስማማው – ከአርባምንጭ ጣቢያችን