የህዳሴው ግድብ ኢትዮጵያውያን በአንድነት ያሳኩት የጋራ ድል መሆኑን የጨታ ወረዳ ነዋሪዎች ገለጹ

የህዳሴው ግድብ ኢትዮጵያውያን በአንድነት ያሳኩት የጋራ ድል መሆኑን የጨታ ወረዳ ነዋሪዎች ገለጹ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 21/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የህዳሴ ግድብ ኢትዮጵያውያን በአንድነት ያሳኩት የጋራ ድል መሆኑን በካፋ ዞን የጨታ ወረዳ ነዋሪዎች ተናገሩ።

ግድቡ የኢትዮጵያን የዕድገት ጉዞ ለማሳካት ምሳሌ የሚሆን ነው ብለዋል፡፡

የግንባታውን መጠናቀቅ አስመልክቶ ያነጋገርናቸው የወረዳው ነዋሪዎች መካከል አቶ አብዱልከሪም ጀማል፣ አቶ አትርሴ ክፍሌ እና አቶ እንግዳ ሀይለማርያም ከብዙ ውጣ-ውረድ በኋላ ወደ መመረቅ ደረጃ በመድረሱ መደሰታቸውን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ አሁን ያለው ትውልድ በቁርጠኝነት ያሳካው ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸው፥ ግድቡ የኢትዮጵያ ህዝብ በትብብር እውን ያደረገው ትልቅ ፕሮጀክት መሆኑን አንስተዋል።

በመተባበር ሀገራዊ ዕቅዶችን ማሳካት እንደሚቻል ያስመሰከረ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡

ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለሀገር ኢኮኖሚ ትልቅ ትርጉም እንደሚኖረው ያመላከቱት አስተያየት ሰጪዎቹ፥ ኢትዮጵያ ተጽዕኖ ፈጣሪ ሀገር እንድትሆን ያስችላታል ብለዋል፡፡

ከዚህ ትምህርት በመውሰድ በቀጣይ ሌሎች ትልልቅ ሀገራዊ ፕሮጀክቶችን ለማሳካት በአንድነት መቆም እንደሚገባ ተናግረዋል።

ዘጋቢ፡ ሀብታሙ ታደሰ – ከቦንጋ ጣቢያችን