ነጋዴው ማህበረሰብ በወቅታዊ ሁኔታዎች ሳይሸበር ኑሮን በማረጋጋት ለመንግስት ያለውን አጋርነት ሊያረጋግጥ እንደሚገባ በደቡብ ኦሞ ዞን የሳላማጎ ወረዳ አስተዳደር አስታወቀ‎

ነጋዴው ማህበረሰብ በወቅታዊ ሁኔታዎች ሳይሸበር ኑሮን በማረጋጋት ለመንግስት ያለውን አጋርነት ሊያረጋግጥ እንደሚገባ በደቡብ ኦሞ ዞን የሳላማጎ ወረዳ አስተዳደር አስታወቀ‎

‎ወቅታዊ የንግድ ዋጋ ሁኔታና በከተማው ለሚከናወነው የኮሪደር ልማት የነጋዴውን ማህበረሰብ አስተዋጽኦ በማጠናከር የጋራ መግባባት ለመፍጠር ያለመ ምክክር በሃና ከተማ ተካሂዷል።‎

‎የወረዳው ንግድና ገበያ ልማት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ኩሻቦ ኩሲያ እንደገለፁት፤ በወረዳው የንግድ ሥርዓቱን ለማሻሻል እንደ መንግሰት የቁጥጥርና የክትትል ሥርዓቱን በማጠናከር በርካታ ሥራዎች ሲሰሩ መቆየታቸውን አስታውሰዋል።‎

‎ይሁን እንጅ አሁን ላይ በተለያዩ ወቅታዊ ሁኔታዎች ምክንያት በነጋዴው ማህበረሰብ የሚስተዋሉ የሚዛን ማጭበርበር፣ ህገ-ወጥ የመንገድ ዳር ንግድና ግብይት፣ ከንግድ ፍቃድ ውጪ መነገድና ሌሎችም የሙስና አመለካከቶች እና ድርጊቶች ሊታረሙ እንደሚገባ አፅንኦት ስጥተዋል።‎

‎የሳላማጎ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ህጉ ቅጣቱ በበኩላቸው፤ ለውጥ ማምጣት የሚቻለው ልማትን በማረጋገጥ በመሆኑ ከሙስና የፀዳ ፍትሐዊ፣ አሳታፊ፣ ተአማኒ የሆነ ሥርዓት በመዘርጋት እየተሠራ መሆኑን ገልፀዋል።‎

‎በመሆኑም ነጋዴው የማህበረሰቡ ልማቱ አንድ አካል እንደመሆኑ በወቅታዊ ሁኔታዎች ሳይሸበር ኑሮን በማረጋጋትና በሌሎችም ልማቶች ለመንግስት ያለውን አጋርነት በማረጋገጥ ሊሰራ ይገባል ብለዋል።‎

‎እንደ ወረዳ የቁጥጥርና ክትትል ሥርዓት ክፍተት፣ ህገ-ወጦችን አስተማሪ ቅጣት ከመቅጣት አንፃር ያሉ ክፍተቶችና ሌሎችም ጉዳዮች ላይ እንደ መንግስት ትልቅ ትኩረት የሚሹ ስለመሆናቸው ተሳታፊዎች አንስተዋል።‎

‎የመድረኩ መሪዎችም እንደ ተቋም ከሰው ኃይልና ሌሎችም አንፃር ክፍተቶች ቢኖሩም ነጋዴው በተግባባው ልክ በጋራ በትብብር እና በቅንጅት መስራት ከቻለ ለውጥ ማምጣት እንደሚቻል በማመን ሊሰራ እንደሚገባ ገልጸዋል።‎

‎አንዳንድ ጊዜ ከጂንካ-ሃና መንገድ ላይ በህጋዊ ነጋዴ ማህበረሰብ ላይ የሚስተዋሉ ያልተገቡ መጉላላቶች ተገቢ ባለመሆናቸው ተቋሙና የወረዳው አስተዳደር ከዞኑ የሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር እየሠራ መሆኑን ኃላፊዎቹ ገልፀዋል።‎

‎ዘጋቢ: ከተማ በየነ – ከጂንካ ጣቢያችን