የትምህርት ቤቶችን የትምህርት ግብዓት ችግር ለመቅረፍ የውስጥ ገቢ አቅምን የማሳደግ ስራ እየተሠራ እንዳለ ተገለፀ

የትምህርት ቤቶችን የትምህርት ግብዓት ችግር ለመቅረፍ የውስጥ ገቢ አቅምን የማሳደግ ስራ እየተሠራ እንዳለ ተገለፀ

በኣሪ ዞን ደቡብ ኣሪ ወረዳ ባሉ ትምህርት ቤቶች የተጀመረው የሰብልና ፍራፍሬ ልማት የውስጥ ገቢን ከማሳደግ በተጨማሪ ትምህርት ቤቶች የግብርና ቴክኖሎጂ ማሸጋገሪያ እየሆኑ እንዳሉ ተመላክቷል።

የመማር ማስተማር ስራ የሚጠበቀውን ውጤት እንዲያመጣ ብሎም የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ ዘርፉ ያልተቋረጠ የበጀት እና ቁሳቁስ ድጋፍ እንደሚያስፈልገውም ተገልጿል።

የበጀትና የትምህርት ግብዓት እጥረት በመማር ማስተማር ስራቸው ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ እያሳደረ እንደሚገኝ የሚናገሩት በኣሪ ዞን የደቡብ ኣሪ ወረዳ የተለያዩ ትምህርት ቤቶች ርዕሳነ መምህራን ችግሩን ለመቅረፍ በትምህርት ቤታቸው የሚገኙ ትርፍ መሬቶች ላይ ህብረተሰቡን በማስተባበር የፍራፍሬ እና በቆሎ ሰብል እያመረቱ እንደሚገኙ ገልፀዋል።

የደቡብ ኣሪ ወረዳ ትምህርት ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ካሳሁን አሰግድ በበኩላቸው፤ በወረዳው በ2017 ትምህርት ዘመን ባሉ 60 ትምህርት ቤቶች ከ40 ሺህ በላይ ተማሪዎችን ተቀብሎ እያስተማረ እንደሚገኝ አስረድተው በትምህርት ቤቶቹ የውስጥ ገቢ አቅም ማነስ በትምህርት ጥራቱ ላይ ጫና እያሳደረ እንደሚገኝ ገልፀዋል።

ችግሩን ለመቅረፍ ከወረዳው አስተዳደር ጋር በመተባበር በህብረተሰብ ተሳትፎ በሁሉም ትምህርት ቤቶች የውስጥ ገቢ አማራጮች ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ እንዳለ አስረድተዋል።

የደቡብ ኣሪ ወረዳ ግብርና ጽ/ቤት ኃላፊና የወረዳው ምክትል አስተዳዳሪ አቶ አሸናፊ ደይዳቅ እንደገለፁት፤ በወረዳው በበልግ ምርት ዘመን እየለማ ካለው 24 ሺህ ሄክታር መሬት ውስጥ 10 በመቶ የሚሆነው በተቋማት እንደተሸፈነና በተቋማት የተጀመረው የግብርና ስራ የውስጥ ገቢያቸውን ከማሳደግ ባለፈ የቴክኖሎጂ ማሸጋገሪያ ለማድረግ ታቅዶ እየተሠራ ይገኛል።

ዘጋቢ፡ መልካሙ ቡርዝዳቦ – ከጂንካ ጣቢያችን