ዜጎች የራሳቸውን ጤና ማምረት እንዲችሉ የጤና ማጎልበትና የበሽታ መከላከል ሥራ ላይ የሚዲያ ተግባር ላቅ ያለ መሆኑ ተገለጸ
ሀዋሳ፡ ሰኔ 18/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) ዜጎች የራሳቸውን ጤና ማምረት እንዲችሉ፣ የጤና ማጎልበትና የበሽታ መከላከል ሥራ ላይ የሚዲያ ተግባር ላቅ ያለ መሆኑን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ ኢብራሂም ተማም አስታወቁ፡፡
በክልሉ ታርጫ ከተማ ከክልሉ በየደረጃው ለሚገኙ ለሚዲያና ኮሙኒኬሽን ዘርፍ ባለሙያዎች በጤና ተግባቦት ዓላማ ላይ ያተኮረ ሥልጠና እየተሰጠ ይገኛል።
የክልሉ ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ ኢብራሂም ተማም እንደገለጹት፤ በየደረጃው የሚገኙ ሚዲያዎችና የሚዲያ ባለሙያዎች ለኅብረተሰቡ ተጨባጭ መረጃ መስጠት እንዲችሉ ለማድረግ ታስቦ የተዘጋጀ ሥልጠና ነው።
የሚዲያው ዘርፍ ባለፉት ጊዜያት አስቸኳይ የጥንቃቄ መልዕክቶችን በማስተላለፍ ረገድም የድርሻቸውን እየተወጡ መቆየታቸውንም በማስታወስ።
በክልሉ በጤና መከላከልና ማጎልበት ዘርፍ የዘመቻ ሥራ ሲኖር ተግባቦቱ እንዲኖር ለማስቻል በክልሉ በሚገኙ የደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ቅርንጫፍ ጣቢያዎች በ12 ቋንቋዎች ትርጉም ያላቸው መልዕክቶች እንዲተላለፉ እየተሠራ እንዳለም ገልጸዋል።
በማናቸውም የጤና ልማት ዘርፍ የሚተላለፈውን የመልዕክት ይዘት በመረዳት በተዛቡ አስተሳሰቦች ሳቢያ በኅብረተሰቡ ዘንድ የሚፈጠረውን መረበሽ ለማስቀረት መረጃ በማሰባሰብና በመተንተን ግልጽኝነትን ለመፍጠር አስተማማኝ የመረጃ ምንጭ በመሆን የድርሻቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል።
የወረርሽኝ ቁጥጥርና ግንዛቤ የመፍጠር ሥራ ላይ እና የጤና አጀንዳዎችን ከማሣካት ረገድ የታዩ ክፍተቶች ለማረም፣ ጠንካራ ጎኖችን ለማስቀጠል እንዲቻል ከሥልጠናው የተሻለ ግብኣት ይገኛል ተብሎ እንደሚታሰብም ገልጸዋል።
የሥልጠናው ሰነድ ቀርቦ ውይይት በሰፊው እንደሚደረግም ይጠበቃል።
ዘጋቢ፡ መሣይ መሠለ – ከዋካ ጣቢያችን

More Stories
በክልሉ በ5ኛ ዙር የተቀናጀ የፖሊዮ ክትባት ዘመቻ ከ6 መቶ ሺ በላይ ህፃናት ተጠቃሚ ይሆናሉ
በክልሉ 5ኛው ዙር የተቀናጀ የፖሊዮ ክትባት ዘመቻው በክልሉ ከ 1.1ሚሊየን በላይ ህፃናት የክትባት መርሐግብሩ ተጠቃሚ ይሆናሉ
በኮንታ ዞን አመያ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል የእናቶች እና ህፃናትን ሞት ለመቀነስ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ እንደሚገኝ ተገለፀ