ከልማት አጋሮች የሚገኘውን የበጀት ድጋፍ ለታለመለት አላማ በማዋል ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ እንደሚገባ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግስት ፋይናንስ ቢሮ ገለጸ

ከልማት አጋሮች የሚገኘውን የበጀት ድጋፍ ለታለመለት አላማ በማዋል ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ እንደሚገባ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግስት ፋይናንስ ቢሮ ገለጸ

ቢሮው ለone wash እና co-wash ፕሮግራሞች ተጠቃሚ ለሆኑ ዞኖችና፣ ልዩ ወረዳዎች ፋይናንስ ሴክተር ለሚሰሩ የፕሮግራሙ አካውንታንቶችና አመራሮች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና በወልቂጤ ከተማ እየሰጠ ይገኛል።

የጉራጌ ዞን ፋይናንስ መምሪያ ኃላፊ አቶ አብዶ ሀሰን በእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግራቸው፤ በone wash እና co-wash የሚተገበሩ ፕሮግራሞች እንደ ፋይናንስ ሴክተር ትልቅ አጋዦች ናቸው ብለዋል።

ከረጂ አካላት የምናገኛቸው እገዛዎች በአግባቡ ተግባር ላይ እንዲውሉ የተጣለብንን ኃላፊነት በተገቢው ልንወጣ ይገባልም ብለዋል።

በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ፋይናንስ ቢሮ በመንግስት ፋይናንስ ዘርፍ የቻናል አንድ ፕሮግራሞች ማስተባበሪያ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ታረቀኝ ኑራሙ በሥልጠናው መክፈቻ ወቅት እንዳሉት፤ ሁለቱም ፕሮግራሞች በውኃና ሳኒቴሽን ላይ ትኩረት አድርገው ይሰራሉ። የበጀት ምንጫቸውም 85 በመቶው በአጋር አካላት ድጋፍ ሲሆን ቀሪ 15 በመቶው ደግሞ በኢትዮጵያ መንግስት የሚሸፈን ነው።
በመሆኑም ከአጋር አካላት የሚገኘውን የበጀት ድጋፍ ለታለመለት አላማ በማዋል ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ የፋይናንሱ ሴክተር ኃላፊነት በመሆኑ በትኩረት መስራት እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል።

በሥልጠናው የone wash እና co-wash ፕሮግራሞች ተጠቃሚ ከሆኑ ዞኖችና፣ ልዩ ወረዳዎች ፋይናንስ ሴክተር ለሚሰሩ የፕሮግራሙ አካውንታቶችና አመራሮች እየተሳተፉ ይገኛል።

ዘጋቢ፡ ተረፈ ሀብቴ – ከወልቂጤ ጣቢያችን