የቢሮ ምክትል ሃላፊ ዶ/ር አደገ አለሙ በክልሉ ማዕከላዊና ሰሜን ሲዳማ ዞኖች ዳሌ እና ሸበዲኖ ወረዳ በዶሮ ልማት ስራ የተሰማሩ አርሶ አደሮችን ከግብርና ሚንስቴር ከመጡ ከፍተኛ ባለሞያዎች ጋር ምልከታ አድርገዋል።
በመስክ ምልከታ ወቅት በጤዲቻና መሲንቾ ሜዳ ቀበሌ ዶሮን ከራስ ምግብነት ባለፈ ለገበያ በማቅረብ ጭምር አርሶ አደሮች ምርታማነታቸውን እያረጋገጡ እንደሚገኙም ገልጸዋል።
ካለፉት ሦስት ዓመት ወዲህ የሌማት ቱሩፋት መርሐ ግብር በክልሉ አበረታች ስራ እየተሰራ መሆኑን የጠቀሱት ም/የቢሮው ሃላፊው አምራቹን ሐይል ከተጠቃሚው ጋር የማገናኘት ስራ በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል።
እንደ ሃገር ያጋጠመውን የመኖ አቅርቦት እጥረትን ለመቀነስ ክልሉ ከግብርና ሚንስቴር ጋር ተነጋግሮ ዘላቂ መፍትሄ እስኪገኝ ድረስ: አርሶ አደሩ በቤት ውስጥ የሚመገበውን የተራረፈ ምግብ በጥንቃቄ ለዶሮ መኖነት መጠቀም እንዲችል ጠይቀዋል።
በግብርና ሚንስቴር የዶሮ ልማት ሃብት ዴስክ ሃላፊ ዮናታን ዘውዴ በበኩላቸው የዶሮን ምርታማነት ለመጨመር የተለያዩ የዶሮ አረባብ ዘዴዎችን በመጠቀም በክልሉ የተሰራው ተግባር ውጤታማ መሆኑን ተናግረዋል።
በሚንስቴር መስርያ ቤቱ የተያዘውን “አርሶ አደሩን የሚመስል መንደር” የመፍጠር ዕቅድ ዕውን ያደረገ እንቅስቃሴ መመልከት መቻላቸውንም አንስተዋል።
የእንስሳት መኖ አቅርቦትን ጨምሮ እንቁላል ጣይና ቄብ ዶሮዎችን አሳድጎ ለአርቢዎች የማከፋፈል ስራ እየተሰራ መሆኑን የገለጹት በሐዋሳ ሱፐር ኦቫ አግሮ ቴክ የእንስሳት ሐኪም ዶ/ር ፈቃዱ ኡርጋ የህብረተሰቡን የእንቁላል ፍላጎት ለማርካት መሰራቱን ገልጸዋል።
አርሶ አደሮች በበኩላቸው ምርታማነታቸውን ይበልጥ ለማሳደግ የእንስሳት መኖ አቅርቦት ችግር እንዲቀረፍ ሲሉም ጠይቀዋል።
ዘጋቢ :በምህረተአብ እስራኤል
More Stories
በመላው ሀገሪቱ በቀጣይ ጊዜያት 50 ሞዴል ትምህርት ቤቶች ለመገንባት እየተሰራ ነው መሆኑን የኢፌዲሪ ትምህርት ሚኒስትር ብርሀኑ ነጋ (ፕ/ር) ገለጹ
ተወዳዳሪ ዜጋ እንድትሆኑ ሳትሰርቁ ጠንክራችሁ ፈተናችሁን በራሳችሁ ሥሩ – ብርሀኑ ነጋ (ፕ/ር)
በክልሉ እየተስተዋለ ያለው ህገ-ወጥ የህጻናት የጉልበት ብዝበዛና ፍልሰት ዘርፈ ብዙ ችግር እያስከተለ ነው -አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር)