“በVAR ላይ እምነት የለኝም!” – ፔፕ ጋርዲዮላ
የማንቸስተር ሲቲው አሰልጣኝ ፔፕ ጋርዲዮላ የዘንድሮውን የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫ ለማንሳት በቪዲዮ ረዳት ዳኛ (VAR) ላይ ሳይሆን በራሳቸው ተጫዋቾች ብቃት ላይ ብቻ እንደሚተማመኑ ተናገሩ።
አርሰናል በሳምንቱ መጨረሻ በዌስትሃም ላይ ባገኘው አወዛጋቢ የVAR ውሳኔ የታገዘ ድል የነጥብ ልዩነቱን ወደ አምስት ካሰፋ በኋላ፣ ጋርዲዮላ በስርዓቱ ላይ ያላቸውን ቅሬታ አሰምተዋል።
“VAR ወደ እግር ኳሱ ከመጣበት ጊዜ ጀምሮ አንድም ቀን አምኜው አላውቅም፤ የሳንቲም ዕጣ እንደመጣል ነው” ሲሉ ጋርዲዮላ ስጋታቸውን ገልጸዋል።
ሲቲ ባለፉት ሁለት ተከታታይ የኤፍኤ ካፕ የፍፃሜ ጨዋታዎች ላይ በVAR ውሳኔዎች ተበድሎ ዋንጫ ማጣቱን ጋርዲዮላ አስታውሰዋል።
በተለይም በ2024 ከማንቸስተር ዩናይትድ ጋር በተደረገው ጨዋታ ሊሳንድሮ ማርቲኔዝ በኤርሊንግ ሃላንድ ላይ የሰራው ጥፋትና ባለፈው ዓመት የክሪስታል ፓላሱ ግብ ጠባቂ ዲን ሄንደርሰን ከሳጥን ውጭ ኳስ በእጅ ነክቶ ሳይሰረዝ መቅረቱ አሁንም ድረስ አልተረሳቸውም።
“እኛ ማድረግ የምንችለው ነገር ቢኖር ራሳችንን ማሻሻል ብቻ ነው። በዳኞች ወይም በVAR ላይ ማማረር ትኩረትን ይበትናል” ሲሉ ለተጫዋቾቻቸው መመሪያ አስተላልፈዋል።
አርሰናል ዌስትሃምን 1ለዐ ሲያሸንፍ፣ ካለም ዊልሰን በመጨረሻው ደቂቃ ያስቆጠረው ግብ በVAR ውሳኔ መሰረዙ መድፈኞቹን ለዋንጫው በእጅጉ አቅርቧቸዋል።
ማንቸስተር ሲቲ ዛሬ ምሽት በኢቲሃድ ስታዲየም ክሪስታል ፓላስን ካላሸነፈ፣ አርሰናል ዋንጫውን ለማንሳት የአንድ ጨዋታ ድል ብቻ ነው የሚቀረው።
ዘጋቢ፡ ሙሉቀን ባሳ

More Stories
የአርሰናል የድል ጉዞ እና የዌስትሃም ቁጭት!
ኢትዮጵያ በዛሬው ዕለት ግብፅን ትገጥማለች
የአርሰናል የኋላ ደጀን ቤን ዋይት የውድድር ዓመቱ በጉዳት ተጠናቀቀ