በወላይታ ዞን ባለፉት 10 ወራት ውስጥ ህገ-ወጥ ንግድና ለመከላከል በተደረገው ክትትል 2 ሺህ 135 ነጋዴዎች ላይ የእርምት እርምጃ መውሰድ መቻሉን የዞኑ ንግድና ገበያ ልማት መመሪያ አስታወቀ

የዞኑ ንግድና ገበያ ልማት መመሪያ ሀላፊ አቶ ሀይሌ ሥላስ እንደሚሉት፤ የንግዱና ሥርዓት በማዘመን ህጋዊ የንግድ ሂደት ለመዘርጋት በዞኑ ሁሉም አካባቢዎች ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ ይገኛል።

በዞኑ አንዳንድ አካባቢዎች በህገወጥ የንግድ ሥራ የተሰማሩ ነጋዴዎች በሸማቹ ህብረተሰብ ላይ እያደረጉ ያሉትን ኢኮኖሚያዊ ጫናን ለመቀነስ በዞን ደረጃ የቁጥጥር ግብረ ሀይል ተቋቁሞ እየተሰራ እንደሆነም ጠቁመዋል።

በዞኑ ባለፉት 10 ወራት ውስጥ ህገ-ወጥ ንግድና ለመከላከል በተደረገው ጠንካራ ክትትል 2 ሺህ 135 ነጋዴዎች ላይ የእርምት እርምጃ መውሰድ መቻሉንም አብራርተዋል፡፡

በተለይም የቤንዚን ኮንትሮባንድ ንግድ ጋር ያለውን ህገወጥነት በተገቢው ለመቆጣጠር ከፀጥታ አካላት ጋር በተደረገው ጥረት አበረታች ውጤት ማስመዝገብ መቻሉንም አክለዋል።

በዚህም ባለፉት 10 ወራት ውስጥ 280 ሺህ ሊትር በላይ የኮንትሮባንድ ቤንዚን በቁጥጥር ሥራ ማዋል መቻሉንም አቶ ሀይሌ ጠቁመዋል።

የቤንዚን ችርቻሮ ንግድ ላይ የተሰማሩ ነጋዴዎች በሸማቹ ህብረተሰብ ላይ እንደፈለጉ የዋጋ ጭማሪ የሚያደርጉበትን ሁኔታ ለመከላከል ከተጠቃሚዎችና ከማደያ ባለቤቶች ጋር ውይይት መደረጉንም ገልፀዋል።

በዚህም የህገወጥ የቤንዚን ንግድ በመጠኑ መቆጣጠር መቻሉን አብራርተዋል።

እርምጃ የተወሰደባቸው ህገወጥ የዋጋ ጭማሪ ያደረጉ ፣ ያለንግድ ምዝገባና ፈቃድ የሚንቀሳቀሱ፣ ከተሰማሩበት የንግድ ዘርፋቸው ውጭ የሚሰሩና በኮንትሮባንድ ንግድ የተሰማሩ ህገ-ወጦች መሆናቸውን የተናገሩት በመምሪያው የሸማቾች ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ ብርሃኑ ባልጣ ናቸው።

የሸማቹን ህብረተሰብ መብት ለማስጠበቅ ከንግዱ ማህበረሰብ ጋር ውይይት በማድረግ ህብረተሰብ የማንቃት ሥራ እየተሰራ መሆኑን አቶ ብርሃኑ ጠቁመዋል።

ባለፉት 10 ወራት ውስጥ በተደረገው ሁሉአቀፍ የኢንስፔክሽን ሥራ 44 ሺህ 290 በላይ የንግድ ተቋማት ምልከታ መደረጉንም ቡደን መሪው ገልፀዋል።

ዘጋቢ፡ በቀለች ጌቾ – ከዋካ ጣቢያችን