የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቡና ማህበር በኣሪ ዞን ለሚገኙ የቡና ንግድ ዘርፍ ማህበራትንና የግል ነጋዴዎችን ድጋፍ መሠረት ያደረገ የጋራ የምክክር መድረክ በጂንካ ከተማ አካሂዷል።
የኣሪ ዞን ቡናና ቅመማ ቅመም ጽህፈት ቤት ኃላፊ ወ/ሮ ርብቃ እሳቱ በንግግራቸው፤ በዞኑ 29 ሺህ ሄክታር ቡና እንደሚለማና ዘርፉ ያለውን ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የአርሶ አደሩን ጨምሮ ሁሉንም በሚጠቅም መንገድ በራሱ ስያሜ እንዲሄድ በማዘመን በማህበር መስራት አሰፈላጊ መሆኑን አንስተዋል።
አክለውም የቡናችንን ምርትና ምርታማነት በመጨመር የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በመትከል ምርቱን በማስፋት ነጋዴው፣ አቅራቢው ብሎም አርሶ አደሮች ሞዴል ሆነው ራሳቸው ላኪና አቅራቢ እንዲሆኑ ለማስቻል መደራጀቱ አሰፈላጊ መሆኑን ገልፀዋል።
ይህ አደረጃጀትም ለላቀ ለውጥና ብልጽግና ብሎም የአቅራቢ ነጋዴዎችን መብትና ግዴታ አውቀን ማስጠበቅ እንድንችልና ከሌሎች ጋር ተወዳዳሪ እንድንሆን ይረዳል ብለዋል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቡና ነጋዴዎች ማህበር ኘሬዝዳንት አቶ ዳንኤል ምጃኔ እንደገለፁት፤ በዋናነት በዘርፉ ያሉ የኮንትሮባንድ እንቅሰቃሴዎችን በመግታት ቡናዎች አካባቢውን በሚገልጹ የራሳቸውን ልዩ ጣዕም ይዘው እንድቀርቡ በመሰራት ለጥራት የሚከፈለውን ዋጋ አቅራቢ ነጋዴዎች ከፍለው የአርሶ አደሩን የግንዛቤ ክፍተት በማገዝ ሊስሩ ይገባል።
በሀገራችን በስያሜያቸው ከሚታወቁት ውጪ ሌሎችንም በማሳወቅ ቡናችንን ከፍ ለማድረግ ጥራት ላይ በማተኮር በቅንጅት እንዲሰራ ያሳሰቡት ደግሞ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቡና ነጋዴዎች ማህበር ምክትል ኘሬዝዳንት አቶ ዳመነ ኃይሌ እና የክልሉ የክላስተር አስተባባሪ አቶ አየለ ለልሻ ናቸው።
ለተሳታፊዎች አጠቃላይ ስለማህበሩ አላማና ተግባራት ገለፃ የተደረገላቸው ሲሆን፤ ከተሳታፊዎችም የተለያዩ ጥያቄና አሰተያየቶች ተነስተው በመድረኩ መሪዎች ምላሽና ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል።
በመጨረሻም ስድስት አባላት ያሉት የዞኑ የቡና ነጋዴዎች ማህበር ተቋቁሟል።
ዘጋቢ: ከተማ በየነ – ከጂንካ ጣቢያችን

More Stories
የቅድመ በሽታ መከላከል ተግባራትን በአግባቡ በመፈፀም ጤናማ ትውልድ ለመፍጠር በሚደረጉ ጥረቶች ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ ተገለፀ
የሸዋል ዒድ (ቀሊ ፍቼ) ባህላዊ ስርዓት በስልጤ
ሁሉም ሰው ዴሞክራሲያዊ መብቱን ተጠቅሞ በቀጣይ የሚያስተዳድረውን መንግስት መምረጥ እንዲችል የምርጫ ካርድ በወቅቱ መያዝ እንደሚጠበቅበት ተገለጸ