በማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን አገልግሎት ተጠቃሚ መሆናቸውን የኢሠራ ወረዳ ተገልጋዮች ተናገሩ
የወረዳው አስተዳደር በበኩሉ የማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን አገልግሎት ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጿል።
በኢሠራ ወረዳ ባሌ ጤና ጣቢያ ያነጋገርናቸው ተገልጋዮች የማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን አባላት ሲሆኑ በአገልግሎቱ ደስተኞች መሆናቸውን ተናግረዋል።
የማህበረሰብ አቀፍ ጤና አገልግሎት ከተጀመረበት አንስተው አገልግሎት እያገኙ መሆናቸውን ጠቁመው በተመዘገቡት የአባልነት ካርድ ሙሉ ቤተሰብ እየታከመ መሆኑንም አንስተዋል፡፡
በመድኃኒት እጥረትና አገልግሎት አስጣጥ ላይ የሚስተዋሉ ችግሮች እንደፈቱ ጠይቀዋል፡፡
የባሌ ጤና አጠባበቅ ጣቢያ ስራአስኪያጅ የሆኑት አቶ አለምሰግድ መኩሪያ በበኩላቸው የማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን አገልግሎት ዙሪያ ለህብረተሰቡ የግንዛቤ ስራ ለመስራት እስከ ቀበሌ የጤና ባለሙያዎችን በመመደብ የተለያዩ ስራዎችን እያከናወኑ መቆየታቸውን ተናግረዋል።
በዚህም በርካታ አዲስ አባላትን በማስመዝገብ እና ለነባሮቹ እድሳት በማድረግ አገልግሎቱን ይበልጥ ለማሳለጥ በመስራት ላይ መሆናቸውን ገልፀዋል።
የወረዳው ጤና ጥበቃ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ገዛኸኝ በየነ በበጀት ዓመቱ 8ሺህ 52 የህብረተሰብ ክፍሎችን የማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን ተጠቃሚ ለማድረግ አቅደው እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
የወረዳው ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሰለሞን ተክሌ ከማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን አገልግሎት እና የአባላት ምዝገባ እንዲሁም የካርድ እድሳት ስራ በተቀመጠው የጊዜ ገደብ ለማጠናቀቅ የወረዳው ባለድርሻ አካላትን በየቀበሌው መድበው ክትትልና ድጋፍ እያደረጉ መሆናቸውን ተናግረዋል
አዘጋጅ፦ አፈወርቅ ኦሹ ከዋካ ጣቢያችን
More Stories
የህብረተሰቡን ጤና ለማጎልበት የዘርፉን ተግባራት በተገቢው ለማሳካት ከምንጊዜውም በተሻለ በቁርጠኝነት እየተሰራ መሆኑን የማዕከላዊ ክልል ጤና ቢሮ አስታወቀ
የህዝቡን የልማት ፍላጎቶች ለማሟላትና መንግስታዊ አገልግሎቶችን በተገቢው ለመስጠት የውስጥ ገቢ ግብርን አማጦ ለመሰብሰብ በልዩ ትኩረት እንደሚሰራ ተገለጸ
በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የዘንድሮ አረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር በይፋ ተጀመረ