የጊቤ ሸለቆ ብሄራዊ ፓርክ ተፈጥሯዊ ይዘቱን ጠብቆ እንዲቆይ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ አሰታወቀ
የፖርኩ የህልውና አደጋን ለመከላከል ያለመ የምክክር መድረክ በወልቂጤ ከተማ ተካሄዶል።
በምክክር መድረክ ላይ የተገኙት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ የቱሪዝም ዘርፍ ም/ቢሮ ኃላፊ አቶ ኑሪ ከድር አንደገለጹት ከቱሪስት መዳረሻዎች አንዱ የሆነው የጊቤ ሸለቆ ብሄራዊ ፓርክ ለዜጎች ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ መስጠት እንዲችሉ የመሰረተ ልማትና ሌሎች የአገልግሎት ሰጪ ተቋማትን ማጠናከር ይገባል።
በተለይም ፓርኩ ከዚህ ቀደም የነበረውን ውስብስብ ችግር ለመቅረፍ ጥናት ተደርጎ የላቀ የቱሪዝም አገልግሎትና የጎለበተ የባህል እሴት ለመፍጠር እቅድ አውጥቶ ወደ ተግባር መገባቱን አስረድተዋል።
ፓርኩ የአከባቢውን ብዝሃ ሕይወት እና የተፈጥሮ ሀብቱን ጠብቆ በዘላቂነት ለትውልድ በማሸጋገር ሂደት የራሱን ሚና እንዲጫወት ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አቶ ኑሪ ገልጸዋል
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ የባህል ዘርፍ ም/ቢሮ ኃላፊ አቶ ደግነህ ቦጋለ በበኩላቸው የጊቤ ሸለቆ ብሄራዊ ፓርክ ተፈጥሮአዊ ይዘቱን ጠብቆ እንዳይቀጥል የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመቅረፍ የሁሉም ርብርብ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል ።
ፓርኩን በአግባቡ መጠበቅና ማልማት ከተቻለ የሀገር ውስጥና የውጭ ሃገር ቱሪስቶች ቁጥር ከመጨመር ባለፈ የአከባቢውን ማህበረሰብ ባህልና እሴት በማስተዋወቅ ረገድ ሚናው የጎላ እንደሆነ ጠቁመዋል።
የውይይቱ ተሳታፊዎች በሰጡት አሰተያየት በጊቤ ሸለቆ ብሄራዊ ፓርክ ዙሪያ ላይ የተሻለ ግንዛቤ እንዳገኙ ገልፀው የፓርኩን ህልውና ለመታደግ ትኩረት ሰጥተው እንደሚሰሩ ተናግረዋል፡፡
ብሄራዊ ፓርኩ በህገወጥ እርሻ ወረራ እየደረሰ ያለበትን ጉዳት ለመከላከል መንግስት ልዩ ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንዳለበት ተሳታፊዎቹ ጠይቀዋል።
ዘጋቢ፡- ደጋጋ ሂሶቦ ከወልቂጤ ጣቢያችን

More Stories
የቅድመ በሽታ መከላከል ተግባራትን በአግባቡ በመፈፀም ጤናማ ትውልድ ለመፍጠር በሚደረጉ ጥረቶች ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ ተገለፀ
የሸዋል ዒድ (ቀሊ ፍቼ) ባህላዊ ስርዓት በስልጤ
ሁሉም ሰው ዴሞክራሲያዊ መብቱን ተጠቅሞ በቀጣይ የሚያስተዳድረውን መንግስት መምረጥ እንዲችል የምርጫ ካርድ በወቅቱ መያዝ እንደሚጠበቅበት ተገለጸ