ሂጂራ ባንክ ሚዛን አማን ቅርንጫፍ ታላቁን የረመዳን ወርን ምክንያት በማድረግ በሚዛን አማን ከተማ በሚገኘው አዝሃር መስጂድ በመገኘት በከተማዋ ለሚገኙ አቅመ ደካሞች የኢፍጣር ድጋፎች አድርጓል።
ባንኩ በዕለቱ 75 ለሚሆኑና ለችግር ለተጋለጡ የሕብረተሰብ ክፍሎች ከ100 ሺህ ብር በላይ የሚያወጣ ዱቄትና ዘይት ድጋፍ ማድረጉን አስታውቋል።
በመርሀ ግብሩ ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ምክትል ፕሬዝዳንትና የነስር መስጅድ ኢማም ሼህ አደም መሀመድ፤ ሂጅራ ባንክ የእስላማዊ አስተምህሮቶችን በመተግበር ለችግር የተጋሉጡትን ወገኖች መርዳቱ የሚያስመሰግነው መልካም ስራ መሆኑን ገልጸው በሌሎች ተቋማትም ጅምሩ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል።
በረመዳን ጾም ወር እንዲህ ዓይነት መረዳዳትና ችግረኞችን መደገፍ የእምነቱ አስተምህሮ እና ተግባር በመሆኑ የሚያስደስት ነው ብለዋል።
በሚዛን አማን ከተማ የሚገኘው የአዝሀር መስጅድ ኢማም ሸህ መሀመድ ፈትህ እንደገለፁት፤ በእስልምና ሀይማኖት አስተምህሮ ከተቀመጡት መሰረታዊ ነጥቦች የረመዳንን ፆም መጾም፣ የተቸገሩ ወገኖችን መደገፍና መንከባከብ እንዲሁም ዘካን በአግባቡ ማውጣት ተጠቃሾች ናቸው።
የሂጅራ ባንክ የደቡብ ምዕራብ ዲስትሪክት ስራ አስኪያጅ አቶ ሰይድ መሀመድ በበኩላቸው፤ ባንኩ ከወለድ ነፃ አገልግሎት ለሙስሊሙ ሕብረተሰብ የሚሰጥ ሲሆን እንደሀገር በተለያዩ አካባቢዎች ለችግር የተጋለጡ የህብረተሰብ ክፍሎችንና አቅመ ደካሞችን እየደገፈ እንዳለ ገልጸዋል።
ባንኩ 1446ኛውን የረመዳን ፆም ምክንያት በማድረግ በሚዛን አማን ከተማ በዝቅተኛ ገቢ ለሚተዳደሩ ወገኖች ድጋፍ ማድረጋቸውን አስረድተዋል።
ድጋፉ 75 ለሚሆኑና ለችግር ለተጋለጡ የሕብረተሰብ ክፍሎች ከ100 ሺህ ብር በላይ የሚያወጣ ዱቄና ዘይት ድጋፍ ማድረጋቸውን ገልፀው በቀጣይም ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ጠቁመዋል
በስነ ስርዓቱ ላይ የሀይማኖት መሪዎች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ የሂጅራ ባንክ አመራርና ሰራተኞች ተሳታፊ ሆነዋል።
ዘጋቢ፡ ጦያር ይማም – ከሚዛን ጣቢያችን
More Stories
በካፋ ዞን ጨና ወረዳ በምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮግራም (FSRP) የተከናወኑ የልማት ስራዎች ላይ ከድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ጋር የልምድ ልውውጥ ተደረገ
ሳታ ቴክኖሎጂ እና ቢዝነስ ኮሌጅ በአርባ ምንጭ ካምፓስ በተለያዩ የትምህርት ዘርፎች በመጀመሪያ ዲግሪ እና ቴክኒክና ሙያ ስልጠና መስኮች ያሰለጠናቸውን 2 ሺህ 132 ተማሪዎችን አስመረቀ
በዕቅድ የሚመራ የመፈፀም አቅሙ ያደገ ሲቪል ሰርቫንት ለመገንባት እየተሰራ መሆኑን በደቡብ ኦሞ ዞን የሳላማጎ ወረዳ ሲቪል ሰርቪስ ጽ/ቤት ገለፀ