ለህብረተሰቡ ቀልጣፋ የፍትህ አገልግሎት ለመስጠት ቅንጅታዊ አሰራርን ማጠናከር እንደሚገባ ተገለፀ
የጌዴኦ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤቶች፣ የህዝብ ክንፍና ባለድርሻ አካላት የ2017 በጀት ዓመት የ6 ወር ዕቅድ አፈፃፀም ግምገማ ተካሂዷል፡፡
በመድረኩ የጌዴኦ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ሳሙኤል በፍቃዱ፤ ፍርድ ቤቶች ለማህበረሰቡ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት ፎረም በማቋቋም በተከናወኑ ተግባራት ውጤት መመዝገቡን ተናግረዋል፡፡
በ6 ወር አፈፃፀም የተመዘገቡ ውጤቶችን ይበልጥ በማጠናከር የተስተዋሉ ውስንነቶችን ለማረም በትጋትና በቁርጠኝነት እንደሚሰሩ አቶ ሳሙኤል በመግለፅ ለህብረተሰቡ ቀልጣፋ የፍትህ አገልግሎት ለመስጠት ቅንጅታዊ አሰራርን ማጠናከር ይገባል ብለዋል፡፡
የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ድጋፌ አገዜ፤ የፍትህ ተቋማት ጥምረት በመፍጠር በተከናወነው ተግባር በበጋ የቡና ምርት በሚሰበሰብበት ወቅት የሚፈፀመውን የስርቆት ወንጀል መቀነስ መቻሉን ጠቅሰዋል፡፡
በግምገማ መድረኩ የተሳተፉት የጌዴኦ ዞን የፍትህ መምሪያ ኃላፊ አቶ ብዙአየሁ ዘውዴ እና የዲላ ማረሚያ ተቋም ፖሊስ አዛዥ ኢንስፔክተር ትዕግስት ሮቤ፤ በአፈፃፀሙ ሂደት የታዩ ጉድለቶችን በማረም በቀጣይ የህዝቡን የፍትህ ጥያቄ ለመመለስ የበኩላችንን እንወጣለን ብለዋል፡፡
ዘጋቢ፡ ውብሸት ኃ/ማርያም – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን
More Stories
የልማትና መልካም አስተዳደር ስራዎች የህዝብን ጥያቄ ሊመልስ በሚችል መልኩ ሊሆን እንደሚገባ የሀዲያ ዞን ምክር ቤት አበላት ገለጹ
ምክር ቤቶች ለህዝብ የልማት ተጠቃሚነት በትኩረት ሊሰሩ እንደሚገባ የምዕራብ ኦሞ ዞን ምክር ቤት አስታወቀ
በማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን አገልግሎት ተጠቃሚ መሆናቸውን የኢሠራ ወረዳ ተገልጋዮች ተናገሩ