ሀዋሳ፡ የካቲት 29/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የኢፌዴሪ የፓርላማና የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት አባላት ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍል ተወካዮች ጋር በተለያዩ የልማትና መልካም አስተዳደር ጉዳዮች ላይ ከጌዴኦ ዞን አጠቃላይ ሴክተር ባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት አካሂዷል፡፡
ተወካዮቹ ህብረተሰቡ ለሚያነሷቸው የልማት ጥያቄዎች አፋጣኝ እልባት እንዲሰጥ አሳስበዋል፡፡
በመድረኩ የተሳተፉ አጠቃላይ የዞኑ ሴክተር መስሪያ ቤቶች ማናጅመንት አካላት በመሰረተ ልማት ዝርጋታ በሚስተዋሉ ችግሮች ዙሪያ ውይይት አካሂደዋል፡፡
በጤና አገልግሎት አሰጣጥ፣ በመንገድ ልማትና በውሃ መሥመር ዝርጋታ፣ በመብራትና ቴሌኮሚኒኬሽን አገልግሎት አሰጣጥ፣ ህገወጥ የነዳጅ ግብይትና በሌሎች ዘርፎችም የተስተዋሉ ችግሮች ዙሪያ እልባት እንዲሰጥ የማናጅመንት አባላቱ ጥያቄ አንስተዋል፡፡
የኢፌዴሪ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባልና የመንግስት የልማት ድርጅቶች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ኢንጂነር ስለሺ ኮሬ(ዶ/ር) በሳምንቱ ከህዝቡ ጋር በነበራቸው ውይይትና መስክ ጉበኝት በከተማ ልማትና በግብርናው ዘርፍ የተጀመሩ ሥራዎች በህብረተሰቡ ዘንድ ጥሩ መነቃቃትን እንደፈጠረ ገልጸዋል።
በፌዴራል መንግስት የሚሠራው ዲላ- ቡሌ- ዋጩ መንገድ ፕሮጀክት በካሳ ክፍያ ምክንያት ሥራው እንዳይስተጓገል የዞን፣ የክልልና የፌዴራል ጉዳዩ ሚመለከታቸው አካላት አሠራሩን ተከትለው ድጋፍና ክትትል ሊያደረጉት እንደሚገባ ምክትል ሰብሳቢው አስገንዝበዋል፡፡
በአንዳንድ ወረዳና ከተማ አስተዳደሮች በትምህርትና ጤና ተቋማት የደረጃ ዕድገትና የትርፍ ሰዓት ክፍያ መዘግየት በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ክፍተት እየፈጠረ ስለመሆኑና ችግሩን ለመቅረፍ የሚመለከታቸው አካላት ለጉዳዩ በአፅንኦት እልባት እንዲሰጥ ያሳሰቡት ኢንጂነር ስለሺ ኮሬ (ዶ/ር) ከህብረተሰቡ ለሚነሱ ጥያቄዎች ተገቢውን ምላሽ በመስጠት የተጀመሩት የልማት ሥራዎች ዕቅድ ከግብ እንዲደርስ ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ ጠይቀዋል፡፡
ዘጋቢ፡ ውብሸት ኃ/ማርያም – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
የቅድመ በሽታ መከላከል ተግባራትን በአግባቡ በመፈፀም ጤናማ ትውልድ ለመፍጠር በሚደረጉ ጥረቶች ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ ተገለፀ
የሸዋል ዒድ (ቀሊ ፍቼ) ባህላዊ ስርዓት በስልጤ
ሁሉም ሰው ዴሞክራሲያዊ መብቱን ተጠቅሞ በቀጣይ የሚያስተዳድረውን መንግስት መምረጥ እንዲችል የምርጫ ካርድ በወቅቱ መያዝ እንደሚጠበቅበት ተገለጸ