በገቢ አሰባሰብ ዙሪያ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመቅረፍ የሚያስችል ውይይት ከባለድርሻዎች ጋር ተካሄደ
ሀዋሳ፡ የካቲት 28/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በገቢ አሰባሰብ ዙሪያ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመቅረፍ ከባለድርሻዎች ጋር በቅንጅት እየሠራ መሆኑን የጌዴኦ ዞን ገቢዎች መምሪያ ገለፀ።
መምሪያው በበጀት ዓመቱ በ8 ወራት 1 ነጥብ 3 ቢሊዮን በላይ ብር መሰብሰቡን አስታውቋል፡፡
መምሪያው በበጀት ዓመቱ የተያዘውን ዕቅድ ለማሳካት በዞኑ ከሚገኙት መዋቅሮች ጋር የግብ ስምምነት በመፈራረም ወደ ተግባር መግባቱን የገለፁት የጌዴኦ ዞን ገቢዎች መምሪያ ኃላፊ አቶ ጌቱ ታምሩ ናቸው፡፡
በበጀት ዓመቱ 2 ቢሊዮን 818 ሚሊዮን 382 ሺህ 99 ብር ለመሰብሰብ በእቅድ ቢያዝም ነገር ግን በ8 ወራት ውስጥ 1 ቢሊዮን 343 ሺህ ብር በላይ መሰብሰብ መቻሉን አቶ ጌቱ አስታውቀዋል፡፡
በዞኑ በሚገኙ 8 ወረዳዎችና 5 የከተማ አስተዳደሮች ካሉት መዋቅሮች ጋር በመቀናጀት ያልተሰበሰቡ ውዝፍና የዘመኑ ግብር በመለየት እስከ መጋቢት 15/2017 ዓ/ም ለመሰብሰብ አቅደው ወደ ተግባር መግባታቸውን የተናገሩት ኃላፊው፥ በገቢ አሰባሰብ ዙሪያ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመቅረፍ ከባለድርሻዎች ጋር በቅንጅት እየሠሩ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡
ህብረተሰቡ በግብይት ወቅት ደረሰኝ ጠይቆ እንዲቀበል ያስገነዘቡት አቶ ጌቱ ሁሉም ግብርን በወቅቱ በታማኝነት በመክፈል የዜግነት ግዴታውን እንዲወጣ አሳስበዋል፡፡
ዘጋቢ፡ ውብሸት ኃ/ማርያም – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
በክልሉ የሚገኙ ነዋሪዎችን ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚያስችል ሥራ በትኩረት እየተሠራ እንደሚገኝ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) ገለጹ
የእናቶችንና ጨቅላ ህፃናትን ሞት ለመቀነስ በሚደረጉ ጥረቶች ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ ተገለፀ
የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርእሰ መስተዳደር (ዶ/ር ) እንዳሻው ጣሰው በተገኙበት በጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ምርቃትና የመሰረተ ድንጋይ የማስቀመጥ ስነ-ስረዓት እየተካሄደ ይገኛል