አባቶቻችን ያስመዘገቡትን ድል ለመድገም የአሁኑ ትውልድ አንድነትን በማጠናከር የተጀመሩ የልማት ስራዎች ላይ ትኩረት እንዲያደርግ ተጠየቀ
ሀዋሳ፡ የካቲት 24/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) አባቶቻችን ያሰመዘገቡትን ድል ለመድገም የአሁኑ ትውልድ አንድነትን በማጠናከር የተጀመሩ የልማት ስራዎች ላይ ትኩረት እንዲያደርግ የጌዴኦ ዞን አስተዳደር አስታወቀ፡፡
129ኛው የአድዋ ድል መታሰቢያ በዓል በጌዴኦ ዞን በተለያዩ ዝግጅቶች በዲላ ከተማ በሚችሌ ጀግኖች አደባባይ ላይ ተከብሯል።
የዲላ ከተማ ከንቲባ አቶ ዳንኤል ሽፈራው እንደገለፁት አባቶቻች ቴክኖሎጂ ባላደገበት ልዩነታቸውን ወደ ጎን በመተው አንድነታቸው በማጠናከር የመጣውን ወራሪውን ኃይል በማሸነፍ አንገታችንን ቀና አድርገን እንዲንሄድ አድርገዋል፡፡
የዓድዋ ድል ኢትዮጵያውያን ሲያስተዳድሯቸው ከነበሩ ሥርዓቶች ጋር ችግር ቢኖርባቸውም በሀገራቸው ሉዓላዊነት ላይ የተቃጣን ጥቃት ግን በመመከትና አንድነትን በማጠናከር ያስመዘገቡት ድል የአሁኑ ትውልድ ጠንክሮ በመስራት ድህነትን ለማሸነፍ ትምህርት የሚወስድበት መሆኑን ከንቲባው ገልጸዋል፡፡
የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) የዓድዋ ጦርነት የጥቁሮችን የመሸነፍ ስሜት በመቀየር በፅናት እና በአንድነት በመቆም ብቻ ድል ማድረግ እንደሚቻል በግልጽ ያሳየ መሆኑን ገልጿል።
አድዋ ጀግኖች አባቶች በሰሩት ታላቅ ገድል በአለም አደባባይ ከፍ ብለን እንድንታይ ያደረገ ታላቅ ገድል ነዉ ያሉት አስተዳዳሪው፥ አድዋ ሲዘከር ለትውልዱ የሚያስተላልፈው ትምህርት ከፍተኛ ነው ብለዋል፡፡
የሚችሌ ጀግኖች ለጠላት እጅ ባለመስጠት ዘመናዊ መሳሪያ ሳይታጠቁ ጠላትን በጦርና ጋሻ ብቻ ድል በመንሳት ሀገርን ከወረራ አድኖ ለትውልድ በማስረከባቸው ክብር ይገባቸዋልም ብለዋል።
አባቶቻችን በሰሩት ታሪክ የአሁን ትውልድ ትምህርት በመውሰድ ድህነትንና ተረጂነት በማስወገድ ድሉን ለመድገም አንድነትን በማጠናከር የተጀመሩ የልማት ስራዎች ላይ ትኩረት እንዲያደርግ አስተዳዳሪው አሳስበዋል፡፡
ዘጋቢ፡ ውብሸት ኃ/ማርያም – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
በክልሉ የሚገኙ ነዋሪዎችን ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚያስችል ሥራ በትኩረት እየተሠራ እንደሚገኝ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) ገለጹ
የእናቶችንና ጨቅላ ህፃናትን ሞት ለመቀነስ በሚደረጉ ጥረቶች ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ ተገለፀ
የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርእሰ መስተዳደር (ዶ/ር ) እንዳሻው ጣሰው በተገኙበት በጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ምርቃትና የመሰረተ ድንጋይ የማስቀመጥ ስነ-ስረዓት እየተካሄደ ይገኛል