የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የ2017 ክልላዊ የበልግ አዝመራ ተግባራት የማስጀመሪያ የንቅናቄ መድረክ በዲላ ከተማ እየተካሄደ ነው
ሀዋሳ፡ የካቲት 19/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) “የግብርና ምርታማነት ለብልጽግናችን” በሚል መሪ ቃል የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የ2017 ክልላዊ የበልግ አዝመራ ተግባራት የማስጀመሪያ የንቅናቄ መድረክ በዲላ ከተማ እየተካሄደ ነው።
በማስጀመሪያ የንቅናቄ መድረኩ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጥላሁን ከበደን ጨምሮ የክልሉ ብሔረሰቦች ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ አቶ አዳማ ትንጳዬ፣ የክልሉ የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ገ/መስቀል ጫላ፣ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የስራ እድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር አበባየሁ ታደሰ፣ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የዲላ ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር መሪሁን ፍቅሩ እና ሌሎች የክልሉ የካቢኔ አባላት፣ የዞንና ልዩ ወረዳ የአመራር አካላት እንዲሁም የግብርና ስራ ተዋናዮች ተሳታፊ ሆነዋል።
የንቅናቄ መድረኩን ያስጀመሩት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጥላሁን ከበደ ባደረጉት ንግግር እንደአሉት፤ የዘንድሮ የበልግ አዝመራ የንቅናቄ መድረክ የዝናብ መዘግየት ከመኖሩ ጋር ተያይዞ አሳሳቢና አስጊ ሁኔታ ላይ ሆነን የምናካሂደው ነው።
በተለይ በግብርና ስራ ምርታማነት ላይ እንደ ስጋት የሚጠቀሱት የአየር ንብረት መዛባት፣ የሰብል በሽታ፣ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምና የድህረ ምርት አያያዝን ጨምሮ የገበያና ግብይት ላይ ያሉ ፈተናዎችን ተቋማዊ በሆነ መንገድ በመፍታት ምርታማነትን ማረጋገጥ ያስፈልጋል ተብለዋል።
ለሁሉም የብልጽግና ስኬቶች ቁልፉ የግብርናው ሴክተር እንደሆነ የገለጹት ርዕሰ መስተዳድሩ በየደረጃው ያለው አመራር የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል።
በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማእረግ የዲላ ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር መሪሁን ፍቅሩ በበኩላቸው፤ የግብርናውን ዘርፍ ውጤታማነት ለማረጋገጥ ርብርብ እየተደረገ ስለመሆኑ ጠቅሰዋል።
በዚህም በዘንድሮ የበልግ እርሻ ከ848 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት በላይ በማልማት ከ 77 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት መታቀዱን አስረድተዋል።
በንቅናቄ መድረኩ በበልግ እርሻ የሚከናወኑ ተግባራትን በተመለከተ የመወያያ ጽሁፎች እየቀረቡ ሲሆን ውይይት ይደረግባቸዋል።
ዘጋቢ: ወንድወሰን ሽመልስ

More Stories
አርባምንጭ ዩኒቨርስቲ ሳውላ ካምፓስ ለ9ኛ ጊዜ በተለያዩ የሙያ መስኮች ያሰለጠናቸውን 121 ተማሪዎችን አስመረቀ
ዲግሪው “ወረቀት ብቻ ሳይሆን፣ የሀገር ተስፋና የትውልድ ኃላፊነት ነው” – አፈወርቅ ካሱ (ፕ/ር)
በክልሉ የተጀመሩ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ የድጋፍና ክትትል ስራ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የመጠጥ ውሃና ሳኒቴሽን ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ዶ/ር አስፋው ዲንጋሞ ገለጹ