‎‎”እንዳይረሳ ቅድሚያ ለደኅንነት” በሚል መሪ ቃል የትራንስፖርትና መንገድ ዘርፍ የሕዝብ ንቅናቄ መድረክ ተካሄደ

‎‎”እንዳይረሳ ቅድሚያ ለደኅንነት” በሚል መሪ ቃል የትራንስፖርትና መንገድ ዘርፍ የሕዝብ ንቅናቄ መድረክ ተካሄደ

ሀዋሳ፡ የካቲት 17/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) “እንዳይረሳ ቅድሚያ ለደኅንነት” በሚል መሪ ቃል በጎፋ ዞን ትራንስፖርትና መንገድ ልማት መምሪያ ዞናዊ የ2017 በጀት ዓመት የ6 ወር ዕቅድ አፈፃፀም ግምገማ እና የትራንስፖርትና መንገድ ዘርፍ የሕዝብ ንቅናቄ መድረክ ተካሂዷል።

የትራፊክ አደጋ በሰውና በንብረት ላይ የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቀነስ በትኩረት እንደሚሰራ የዞን ትራንስፖርትና መንገድ ልማት መምሪያ ገለፀ፡፡

የጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ዳግማዊ አየለ እንዳሉት በሀገራችን በበሽታ ከሚሞተው የሰው ቁጥር በላይ በትራፊክ አደጋ ምክንያት የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር ከፍተኛ በመሆኑ በሰው ሕይወት ላይ የሚያስከትለውን የሞት አደጋና የንብረት ውድመት ለመቀነስና ለመከላከል በትኩረት ሊሰራ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

የመንገድ መሠረተ ልማት አለመስፋፋት፣ በአሽከርካሪዎች ዘንድ የሚታዩ የብቃት ማነስ ችግሮችና ጠጥቶ ማሸከርከር የትራፊክ አደጋ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ እንዲመጣ መንስኤ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡

ችግሩን ለመፍታት ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት መስራት እንዳለባቸው አሳስበዋል።

የዞኑ ትራንስፖርትና መንገድ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ጃኬቴ ዛይሴ በበኩላቸው፥ የትራፊክ አደጋ በሰውና በንብረት ላይ እያስከተለ ያለው ጉዳት ከፍተኛ በመሆኑ በየጊዜው የሚከሰተውን የትራፊክ አደጋ ለመቀነስ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በመቀናጀት ተተኪ የሌለውን የሰው ሕይወትና የንብረት ውድመት ለመታደግ መስራት እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡

በመድረኩ የትራፊክና የመንገድ ዘርፍ የስድስት ወራት የሥራ ሪፖርት ሰነድ ቀርቦ ውይይት ተካሄዷል።

የወይይቱ ተሳታፊዎች የትራፊክ ደንብ አከባበር ዙሪያ የመጡ መሻሻሎች አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባ አንስተው በእግረኞች ዘንድ የሚሰተዋሉ የግንዛቤ እጥረቶችን በመቀነስ በአሸክርካሪ ማሰልጠኛ ተቋማት የሚታዩ የመንጃ ፈቃድ አሰጣጥ ችግሮችን በመቀነስና ህብረተሰቡን በማሳተፍ የተሰሩ መሰረተ ልማቶችን መጠበቅ የትኩረት መስኮች በመሆናቸው ለስኬታማነታቸው የድርሻቸውን እንደሚወጡ አስተያዬታቸውን ሰጥተዋል፡፡

‎ዘጋቢ፡ ስንታየሁ መላቱ – ከሳዉላ ጣቢያችን