የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ለማሳደግና ብልጽግናን ለማረጋገጥ በሀገሪቱ ሰላምን ማስፈን እንደሚገባ ተገለፀ
የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ከኢፌዲሪ ሰላም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ”ብሄራዊ ጥቅሞቻችንና ቀጠናዊ ትስስር ለሚዛናዊ የህዝቦች ተጠቃሚነት” በሚል መሪ ሃሳብ የምክክር መድረክ ተካሂዷል::
የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ዳዊት ሃዬሶ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ ብሔራዊ ጥቅሞቻችን ፖሊሲዎች ሲቀየሩ አብረው የሚቀየሩ ሳይሆኑ በፅኑ መሠረት ላይ የተመሠረቱ ናቸው።
ልማትና ብልጽግና ማረጋገጥ የሚቻለው በጋራና በአንድነት ትስስር በመፍጠር ማደግ ሲቻል እንደሆነም ጠቁመዋል::
በውይይት መድረኩ የተገኙት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰላምና የውጭ ግንኙነት ቋሚ ኮሚቴ አባል አቶ አየለ ነገሪ፤ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ለማሳደግና ብልጽግና ለማረጋገጥ ቀጠናዊ ትስስር ማጠናከር ያስፈልጋል ብለዋል::
በመድረኩ መነሻ ጽሁፍ ያቀረቡት በዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የፖሊቲካ ሳይንስና ዓለም ዓቀፍ ግንኙነት ትምህርት ክፍል ኃላፊና ተመራማሪ መምህር ሙሉዓለም ሃ/ማርያም፤ የውይይቱ ዓላማ ብሔራዊ ጥቅሞቻችንን እንድናውቅ፣ በቀጠናዊ ትስስር ምን ዓይነት ተግዳሮቶች አሉ? እንዴት ወደ ትስስር መግባት ይቻላል? በሚሉ ጉዳዮች ላይ ማህበረሰቡን ግንዛቤ ማስጨበጥን ታሳቢ ያደረገ ነው ብለዋል::
ብሄራዊ ጥቅም ለማስከበር መንግስት ብቻ ሳይሆን ከግለሰብ ጀምሮ ተቋማት ጠንካራ ስራ መስረት እንዳለባቸው ተመራማሪው አስረድተዋል።
በሰላም ሚኒስቴር የብሔራዊ መግባባት ባለሙያ አቶ ፋልታሞ ፋካና በበኩላቸው፤ ብሄራዊ ጥቅም ከግል ጥቅም የተሻገረና የሀገርንና የጎረቤት ሀገራትን ክብር ከፍ የሚያደርግ እንደሆነ ገልፀዋል::
ምሁራን ሀገር እንድትበለጽግና የህዝቦች ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ በትኩረት ሊሰሩ እንደሚገባም አቶ ፋልታሞ ጠቁመዋል::
በመድረኩ የተገኙ አንዳንድ ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት እንደነዚህ ዓይነት አጀንዳዎች ብሔራዊ ጥቅሞቻችንንና ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ፋይዳቸው የጎላ ነው ብለዋል::
ዜጎች ለብሔራዊ ጥቅምና ለሀገር ሰላም ዘብ በመቆም የህዝቦች ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ የድርሻቸውን መወጣት እንደለበቸው ተሳተፊዎቹ ጠቅሰዋል::
በመድረኩ የሰላም ሚኒስቴር ተወካዮች፣ ከማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልልና ከሀድያ ዞን የተውጣጡ የሰላምና ፀጥታ ቢሮ ተወካዮች፣ የሀገር ሽማግሌዎችና ምሁራን ተሳትፈዋል።
ዘጋቢ: በየነ ሰላሙ – ከሆሳዕና ጣቢያችን

More Stories
የቅድመ በሽታ መከላከል ተግባራትን በአግባቡ በመፈፀም ጤናማ ትውልድ ለመፍጠር በሚደረጉ ጥረቶች ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ ተገለፀ
የሸዋል ዒድ (ቀሊ ፍቼ) ባህላዊ ስርዓት በስልጤ
ሁሉም ሰው ዴሞክራሲያዊ መብቱን ተጠቅሞ በቀጣይ የሚያስተዳድረውን መንግስት መምረጥ እንዲችል የምርጫ ካርድ በወቅቱ መያዝ እንደሚጠበቅበት ተገለጸ