የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ለማሳደግና ብልጽግናን ለማረጋገጥ በሀገሪቱ ሰላምን ማስፈን እንደሚገባ ተገለፀ
የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ከኢፌዲሪ ሰላም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ”ብሄራዊ ጥቅሞቻችንና ቀጠናዊ ትስስር ለሚዛናዊ የህዝቦች ተጠቃሚነት” በሚል መሪ ሃሳብ የምክክር መድረክ ተካሂዷል::
የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ዳዊት ሃዬሶ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ ብሔራዊ ጥቅሞቻችን ፖሊሲዎች ሲቀየሩ አብረው የሚቀየሩ ሳይሆኑ በፅኑ መሠረት ላይ የተመሠረቱ ናቸው።
ልማትና ብልጽግና ማረጋገጥ የሚቻለው በጋራና በአንድነት ትስስር በመፍጠር ማደግ ሲቻል እንደሆነም ጠቁመዋል::
በውይይት መድረኩ የተገኙት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰላምና የውጭ ግንኙነት ቋሚ ኮሚቴ አባል አቶ አየለ ነገሪ፤ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ለማሳደግና ብልጽግና ለማረጋገጥ ቀጠናዊ ትስስር ማጠናከር ያስፈልጋል ብለዋል::
በመድረኩ መነሻ ጽሁፍ ያቀረቡት በዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የፖሊቲካ ሳይንስና ዓለም ዓቀፍ ግንኙነት ትምህርት ክፍል ኃላፊና ተመራማሪ መምህር ሙሉዓለም ሃ/ማርያም፤ የውይይቱ ዓላማ ብሔራዊ ጥቅሞቻችንን እንድናውቅ፣ በቀጠናዊ ትስስር ምን ዓይነት ተግዳሮቶች አሉ? እንዴት ወደ ትስስር መግባት ይቻላል? በሚሉ ጉዳዮች ላይ ማህበረሰቡን ግንዛቤ ማስጨበጥን ታሳቢ ያደረገ ነው ብለዋል::
ብሄራዊ ጥቅም ለማስከበር መንግስት ብቻ ሳይሆን ከግለሰብ ጀምሮ ተቋማት ጠንካራ ስራ መስረት እንዳለባቸው ተመራማሪው አስረድተዋል።
በሰላም ሚኒስቴር የብሔራዊ መግባባት ባለሙያ አቶ ፋልታሞ ፋካና በበኩላቸው፤ ብሄራዊ ጥቅም ከግል ጥቅም የተሻገረና የሀገርንና የጎረቤት ሀገራትን ክብር ከፍ የሚያደርግ እንደሆነ ገልፀዋል::
ምሁራን ሀገር እንድትበለጽግና የህዝቦች ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ በትኩረት ሊሰሩ እንደሚገባም አቶ ፋልታሞ ጠቁመዋል::
በመድረኩ የተገኙ አንዳንድ ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት እንደነዚህ ዓይነት አጀንዳዎች ብሔራዊ ጥቅሞቻችንንና ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ፋይዳቸው የጎላ ነው ብለዋል::
ዜጎች ለብሔራዊ ጥቅምና ለሀገር ሰላም ዘብ በመቆም የህዝቦች ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ የድርሻቸውን መወጣት እንደለበቸው ተሳተፊዎቹ ጠቅሰዋል::
በመድረኩ የሰላም ሚኒስቴር ተወካዮች፣ ከማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልልና ከሀድያ ዞን የተውጣጡ የሰላምና ፀጥታ ቢሮ ተወካዮች፣ የሀገር ሽማግሌዎችና ምሁራን ተሳትፈዋል።
ዘጋቢ: በየነ ሰላሙ – ከሆሳዕና ጣቢያችን

More Stories
አርባምንጭ ዩኒቨርስቲ ሳውላ ካምፓስ ለ9ኛ ጊዜ በተለያዩ የሙያ መስኮች ያሰለጠናቸውን 121 ተማሪዎችን አስመረቀ
ዲግሪው “ወረቀት ብቻ ሳይሆን፣ የሀገር ተስፋና የትውልድ ኃላፊነት ነው” – አፈወርቅ ካሱ (ፕ/ር)
በክልሉ የተጀመሩ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ የድጋፍና ክትትል ስራ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የመጠጥ ውሃና ሳኒቴሽን ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ዶ/ር አስፋው ዲንጋሞ ገለጹ