የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ምክትል ኃላፊና የኤች አይ ቪ/ኤድስ መከላከልና መቆጣጠር ዘርፍ ኃላፊ አቶ ማቴዎስ ጋርሾ እና የኮሬ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ታረቀኝ በቀለ ዘመቻውን በኬሌ ከተማ በይፋ አስጀምረዋል።
በዞኑ ከ36 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ህጻናት የፖሊዮ ክትባት ለማድረስ ታቅዶ ለሁለት ተከታታይ ወራት ሲሰራ መቆየቱን የተናገሩት የኮሬ ዞን ጤና ዩኒት ኃላፊ አቶ ደመላሽ ሽፈራው፤ በቂ ዝግጅት በመደረጉ የተሸለ ውጤት እንጠብቃለን ብለዋል።
የኮሬ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ታረቀኝ በቀለ በኩላቸው፤ ከአምስት ዓመት በታች ላሉ ህጻናት እየተሰጠ ላለው የተቀናጀ የፖሊዮ ክትባት ዘመቻ የዞኑ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል ብለው ክትባቱ በትኩረት መሠጠት እንዳለበት አመላክተዋል።
በማስጀመሪያ መርሃ ግብር የተገኙት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ምክትል ኃላፊና የኤች አይ ቪ/ኤድስ መከላከልና መቆጣጠር ዘርፍ ኃላፊ አቶ ማቴዎስ ጋርሾ በበኩላቸው፤ የፖሊዮ ክትባት ዘመቻ ዓላማው ከሀገራችን ፖሊዮን ማጥፋት መሆኑን ተናግረው በክልሉ ሁሉም አካባቢዎች እየተሠጠ መሆኑን ገልጸዋል።
አንድም ህጻን ሳይከተብ መቅረት የለበትም ያሉት ምክትል ቢሮ ኃላፊው ለዚህም ነው ዘመቻው ቤት ለቤት እንየተደረገ ያለው ብለዋል።
ከፖሊዮ ክትባት ዘመቻ ጎን ለጎን የህጻናት የምግብ እጥረት፣ የነፍሰ ጡር እናቶች፣ የቆልማማ እግር እና ፖሊዮ የተገኘባቸውም ካሉ የመለየት ስራ የሚሠራ መሆኑን ገልጸዋል።
በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ሌሎች የዞኑና የኬሌ ከተማ አመራሮች እና ባለድርሻ አካላት የተገኙ ሲሆን ዘመቻው ከ14/06/2017 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ አራት ቀናት የሚቆይ ይሆናል።
ዘጋቢ: እስራኤል ቅጣው – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
አርባምንጭ ዩኒቨርስቲ ሳውላ ካምፓስ ለ9ኛ ጊዜ በተለያዩ የሙያ መስኮች ያሰለጠናቸውን 121 ተማሪዎችን አስመረቀ
ዲግሪው “ወረቀት ብቻ ሳይሆን፣ የሀገር ተስፋና የትውልድ ኃላፊነት ነው” – አፈወርቅ ካሱ (ፕ/ር)
በክልሉ የተጀመሩ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ የድጋፍና ክትትል ስራ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የመጠጥ ውሃና ሳኒቴሽን ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ዶ/ር አስፋው ዲንጋሞ ገለጹ