የተለያዩ የልማት ፍላጎቶችንና ጥያቄዎችን ለመመለስ እንዲያስችል የገቢ አፈጻጸሙን በይበልጥ ማሳደግ እንደሚገባ የጋሞ ዞን ገቢዎች መምሪያ አስታወቀ

የተለያዩ የልማት ፍላጎቶችንና ጥያቄዎችን ለመመለስ እንዲያስችል የገቢ አፈጻጸሙን በይበልጥ ማሳደግ እንደሚገባ የጋሞ ዞን ገቢዎች መምሪያ አስታወቀ

‎መምሪያው በ2017 በጀት አመት ሰባት ወራት ከ2 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሠብሰብ መቻሉም ተመልክቷል።

‎”ቃልን ወደ ባህል፤ ጸጋን ወደ ገቢ” በሚል መሪ ቃል የታክስ ንቅናቄ መድረክ በአርባ ምንጭ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።

‎የጋሞ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የዞኑ ገቢዎች መምሪያ ኃላፊ ወ/ሮ ልሳነ ወርቅ ካሳዬ የንቅናቄ መድረኩን በንግግር ሲከፍቱ እንደተናገሩት፤ የተለያዩ የልማት ፍላጎቶችንና ጥያቄዎችን ለመመለስ እንዲያስችል ያሉንን ጸጋዎች በመለየት የገቢ አቅማችንን በይበልጥ ማሳደግ ይገባናል።

‎መምሪያው በበጀት አመቱ 5 ነጥብ 7 ቢሊየን ብር ለመሠብሰብ አቅዶ እየሰራ መሆኑንና በሰባት ወራት 2 ቢሊዮን 652 ሚሊዮን 898 ሺህ 916 ብር ገቢ መሠብሰቡን ተናግረዋል።

‎የዕቅዱ አፈጻጸም ካለን አቅም አንጻር ሲታይ ዝቅተኛ በመሆኑ በቀጣይ ቀሪ ወራት ያለንን አቅም አሟጠን በመጠቀምና ሁሉንም የገቢ አማራጮች በይበልጥ በመለየት መሰብሰብ እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተዋል።

‎ዞኑ ሰላማዊ አካባቢ ከመሆኑ ባሻገር የማዕድናት ክምችት ባለቤት፣ ለኢንዱስትሪና ለኢንቨስትመንት እንዲሁም ለንግድ እንቅስቃሴና ለግብይት ምቹ በመሆኑ የገቢ እቅዱን የተሳካ ለማድረግ በሁሉም መዋቅር በይበልጥ ሊሰራ ይገባል ብለዋል ወ/ሮ ልሳነ ወርቅ።

‎ዘጋቢ፡ ማርታ ሙሉጌታ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን