የቁጠባን ባህል በማሳደግ በዞኑ የዳበረ ኢኮኖሚ መገንባት እንደሚገባ የጌዴኦ ዞን አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) ገለጹ
በይርጋጨፌ ወረዳ ህብረት ሥራ ልማት ጽ/ቤት ዳራሮና ቢፎም የገንዘብ ቁጠባና ብድር ኃላፊነቱ የወሰነ ሁለት ህብረት ሥራ ማህበራት ምስረታና ቁጠባ የማሰባሰቢያ መድረክ አካሂዷል፡፡
መድረኩን በንግግር ያስጀመሩት የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር)፥ የጌዴኦ ህዝብ በቁጠባ የተመሠረተ የሀብት አጠቃቀም ሥርዓት ለበርካቶች ሲያስተምር የቆየ ህዝብ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በመሆኑም በጊዜ ሂደት ውስጥ እየተዳከመ የመጣውን የቁጠባ ባህል ዳግም በማንሰራራት የዳበረ ኢኮኖሚ ለመገንባት በዞኑ ከአምስት መቶ በላይ የነበሩ ማህበራትን በሪፎርም በአዲስ መልክ የማደራጀት ሥራ ማከናወን መጀመራቸውንም ገልጸዋል፡፡
በዛሬው ዕለት በይርጋጨፌ ወረዳ የተጀመረው የኅብረት ሥራ ምስረታውና ቁጠባ የማሰባሰብ ሥራ የአንድ ጊዜ ተግባር አለመሆኑንና አባሉ የሁልጊዜ ተግባር በማድረግ ዞኑንና ሀገሪቱን ከተረጂነት ለማላቀቅ በሚደረገው ሂደት የበኩላቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡
የዞኑ ህብረት ሥራ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ብርሃኑ ተካዬ፤ በወረዳው የነበሩ 29 የህብረት ሥራ ማህበራትን በሁለት ኅብረት ሥራ ማህበራት በማዋቀር ጠንካራ የቁጠባና ብድር ኅብረት ሥራ ለመፍጠር እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የይርጋጨፌ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና ልማት ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ክፍሌ ጂግሦ፤ በሪፎርሙ የኅብረት ሥራ ማህበራት በአዲስ መልክ እንዲደራጅ በተቀመጠው መመሪያ መሠረት በወረዳው በየቀበሌው የነበሩ ማህበራት በሁለት “ዳራሮና ቢፎም ኃላፊነት የተወሰነ የገንዘብ ቁጠባና ብድር መሠረታዊ ኅብረት ሥራ ማህበር” ማቋቋማቸውን ተናግረዋል፡፡
ጠንካራ ኢኮኖሚን ለመገንባት ቁጠባ አስፈለጊ በመሆኑ ህብረተሰቡ ካለው በመቆጠብ በየአካባቢው በተደራጀ በቢፎምና በዳራሮ ቁጠባና ብድር ህብረት ሥራ በመቆጠብ ኢኮኖሚያቸውን በቁጠባ እንዲመሩ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
በዞኑ በአንድ ሳምንት 12 ሚሊዮን የቁጠባ ገንዘብ ለመሰብሰብ እየተሠራ መሆኑ ተመላክቷል፡፡
ዘጋቢ፡ እምነት ሽፈራው – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
ህዝበ ሙስሊሙ የመውሊድ በዓልን ሲያከብር በብዝሃነት ውስጥ የሚንፀባረቁ የመረዳዳትና የአብሮነት በጎ እሴቶችን ይበልጥ በማጠናከር ሊሆን እንደሚገባ ተገለጸ
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልፅግና ፓርቲ ኃላፊና የየዞን ከፍተኛ አመራሮች በሣውላ ማረሚያ ተቋም አረንጓዴ አሻራቸውን በማኖር ልዩ ልዩ የልማት ሥራዎችን ጎበኙ
በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ወረዳ የማህጸን በር ጫፍ ካንሰር ምርመራ እና ልየታ ተካሄደ