በጉራጌ ዞን እንደጋኝ ወረዳ ከ16 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነባው የጭንዳዊየ የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት ግንባታ ተጠናቆ የምረቃ የስነ-ስርዓት እየተካሄደ ነው

ግንባታው የተከናወነው በአካባቢው ተወላጅ ባለሀብት አቶ ዳንኤልን ሱሊቶ እና በአካባቢው ማህበረሰብ ተሳትፎ መሆኑም ተገልጿል።

የአካባቢው ማህበረሰብ ከፍተኛ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት እጥረት የነበረበት ሲሆን ባለሀብቱና ማህበረሰቡ በጋራ በመሆን ባስገነቡት ይህ የጭንዳዊየ የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት 6 ሺህ 500 የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ተመላክቷል።

ዞኑ ከፍተኛ የከርሰ ምድር ውሃ ሀብት ባለቤት ሲሆን ማህበረሰብ፣ ባለሀብትና መንግስት እንዲሁም አጋር ድርጅቶች በመቀናጀት የውሃ አቅርቦት ተደራሽነት ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑም ተጠቁሟል።

በምረቃ ስነ-ስርዓቱ የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ፣ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ውሃና መስኖ ቢሮ ኃላፊ አቶ ዳዊት ኃይሉ፣ የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን የእምድብር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አቡነ ሉቃስ፣ የዞኑ ዋና የመንግስት ተጠሪ አቶ አለማየሁ ገ/መስቀል፣ የዞኑ ምክትል አፈጉባኤ አቶ ኸይሩ መሀመድ እና ሌሎች የዞኑና የወረዳው ከፍተኛ አመራሮች እና ባለሀብቶች እንዲሁም የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።

ዘጋቢ፡ እንዳልካቸው ደሳለኝ – ከወልቂጤ ጣቢያችን