የቁጠባ ባህላችንን በማሳደግ ሁለንተናዊ የኅብረት ሥራ ቤተሰብ ብልጽግና ማረጋገጥ እንደሚገባ ተገለጸ
በጌዴኦ ዞን ኮቾሬ ወረዳ ህብረት ሥራ ልማት ጽ/ቤት “ጊዜው የህብረት ሥራ ማህበራት ነው” በሚል መሪ ቃል ‘ዳራሮ ህብረት ሥራ ማህበር’ ምስረታና የቁጠባ ማሰባሰቢያ መድረክ አካሂዷል፡፡
የኮቾሬ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ጌታቸው ታሪኩ “ዳራሮ ኃላፊነቱ የተወሰነ የገንዘብ ቁጠባና ብድር መሠረታዊ ኅብረት ሥራ ማህበር” የህብረተሰቡን የኑሮ ዘይቤ ለመቀየር ዓላማውን አንግቦ የተቋቋመ ማህበር መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በኅብረት ሥራ ምስረታው ጉባኤ በአንድ ቀን አንድ ሚሊዮን ብር ለመሰብሰብ አቅዶ ቁጠባ የማሰባሰብ ሥራ መጀመሩንም አስተዳዳሪው ተናግረዋል፡፡
የዞኑ ህብረት ሥራ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ብርሃኑ ተካዬ በበኩላቸው፥ በዞኑ ከ134 የገጠር ኅብረት ማህበራት ውስጥ ከ126 በላይ የሚሆኑ ማህበራት በተደረገው ምዘና ከደረጃ በታች በመሆናቸው በአዲስ መልክ ሪፎርም በማካሄድ በዞኑ ከአስር ያልበለጠ ጠንካራ ኅብረት ሥራ ማህበራትን የማደራጀት ሥራ መጀመራቸውን አንስተዋል፡፡
በዚሁ መሠረት በኮቾሬ ወረዳ ዳራሮ የገንዘብ ቁጠባና ብድር መሠረታዊ ኅብረት ሥራ ማህበር በመመሠረት የቁጠባ ገንዘብ የማሰባሰብ ሥራ ማከናወናቸውን አቶ ብርሃኑ ገልጸዋል፡፡
መቆጠብ የገንዘብ ብክነት በማስቀረት፣ ወለድ በማስገኘትና የኅብረት ሥራው በዓመት ከሚያገኘው ጠቅላላ ገቢ ትርፍ ለማግኘት እንደሚያግዝም ኃላፊው አብራርተዋል፡፡
የጌዴኦ ዞን ብልጽግና ፓርቲ ጽ/ቤት ኃላፊና የመንግሥት ዋና ተጠሪ አቶ አበባየሁ ኢሳይያስ በዚህ ወቅት እንደገለጹት ህብረተሰቡ ከድህነት ለማላቀቅ እየተሠራ ባለው እንቅስቃሴ በቁጠባ የተመሠረተ ጠንካራ ኢኮኖሚ መገንባት ለሁለንተናዊ ብልጽግና ማረጋገጥ ወሳኝነት አለው፡፡
ሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች ሀብት በተገቢው መቆጠብ እንደሚያስፈልግ የገለጹት ኃላፊው፥ ህብረተሰቡ አንድነትን በመፍጠርና በኅብረት ሥራ በመቆጠብ ጠንካራ ኢኮኖሚ ለመገንባት የበኩላቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡
በምስረታውና በቁጠባ ገንዘብ ማሰባሰቢያ መድረክ ላይ ተገኝተው ሲቆጥቡ አግኝተን ካነጋገረናቸው መካከል ወ/ሮ ትዕግስት ደያሶ ከሽፎ ቀበሌና አቶ በቀለ ገሎ ከቡኖ ቀበሌ ቁጠባ የዕድገት ሁሉ መሠረት መሆኑን በመጥቀስ ለነገው ብልጽግና ዛሬ ላይ ካላቸው እየቆጠቡ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
ዘጋቢ: እምነት ሽፈራው – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
ህዝበ ሙስሊሙ የመውሊድ በዓልን ሲያከብር በብዝሃነት ውስጥ የሚንፀባረቁ የመረዳዳትና የአብሮነት በጎ እሴቶችን ይበልጥ በማጠናከር ሊሆን እንደሚገባ ተገለጸ
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልፅግና ፓርቲ ኃላፊና የየዞን ከፍተኛ አመራሮች በሣውላ ማረሚያ ተቋም አረንጓዴ አሻራቸውን በማኖር ልዩ ልዩ የልማት ሥራዎችን ጎበኙ
በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ወረዳ የማህጸን በር ጫፍ ካንሰር ምርመራ እና ልየታ ተካሄደ