በትብብር ላይ የተመሰረተ ፉክክር በማጠናከር ተተኪ ስፖርተኞችን ማፍራት እንደሚገባ የሀዲያ ዞን ወጣቶችና ስፖርት መምሪያ ገለፀ
በዞኑ ሆሳዕና ከተማ ለአንድ ሳምንት ሲካሄድ የቆየው የዞኑ ልዩ ልዩ ስፖርት እና የባህል ስፖርት ሻምፕዮና ፍጻሜውን አግኝቷል።
በማጠቃለያ መርሃግብሩ ላይ የተገኙት የዞኑ ወጣቶችና ስፖርት መመሪያ ኃላፊ አቶ ታምሬ ኤርሚያስ፤ ስፖርታዊ ውድድሩ በትብብር ላይ የተመሰረተ ፉክክር በማጠናከር ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ያለመ መሆኑን አንስተው ይህም በፍጹም ስፖርታዊ ጨዋነት በተሞላ መልኩ እና በአንድነት መንፈስ መካሄዱን ተናግረዋል።
ተወዳዳሪዎች በአካላዊ እና በአዕምሮ ጎልብተው ያላቸውን አቅም እንዲያወጡ በማገዝ በተለያዩ ውድድሮች ዞኑን የሚወክሉና የሚያስጠሩ ተተኪዎች እንዲወጡ ዕድል የፈጠረ ስለመሆኑም አውስተዋል።
በመምሪያው የስፖርት ተሳትፎና ውድድር ዘርፍ ቡድን መሪ አቶ መስፍን አበበ በበኩላቸው፤ በውድድሩ በዞኑ ካሉ 20 መዋቅሮች መካከል 6 ወረዳዎችና 4 ከተማ አስተዳደሮች በጠቅላላው 7 መቶ 44 ተወዳዳሪዎች በ14 የስፖርት ዓይነቶች መሳተፋቸውን ገልፀው በተሳትፎው ችሎታቸውን ያሳዩበት እንደሆነም አስረድተዋል።
በቀጣይ ወጥነት ባለው መልኩ በሁሉም የስፖርት ዓይነቶች ማካሄድ እንደሚገባ አስታውሰው፤ የስፖርት ቤተሰብ፣ መንግሥት እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ለስፖርት ዕድገት በትኩረት መስራት ይገባል ብለዋል።
በማጠቃለያው በተካሄደው የወንዶች እግር ኳስ ጨዋታ የአምናው ሻምፕዮን ሆመቾ ከተማ አስተዳደር ከሻሾጎ ወረዳ ጋር ጨዋታ አድርጎ 1 ለ 0 በሆነ ውጤት በማሸነፍ በተከታታይ ዋንጫ ማንሳት ሲችል በሴቶች እግር ኳስ ደግሞ ሆሳዕና ከተማ አስተዳደር የዋንጫ አሸናፊ ሆኗል።
በሌሎች ውድድሮች በአትሌቲክስ በወንዶች እና በሴቶች የምሻ ወረዳ የሜዳልያ አሸናፊ ሲሆን የሌሞ ወረዳ በስፖርታዊ ጨዋነት ተሸላሚ ሆኗል።
በባህላዊ የስፖርት ውድድር በሻህ፣ ቡም እና ገበጣ 12 ጉድጓድ ሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ማሸነፍ ሲችል፤ በገበጣ 18 ጉድጓድ ምስራቅ ባደዋቾ፣ በከርቦ ጊቤ ወረዳ፣ በከርቦ ድብልቅ ደግሞ የፎንቆ ከተማ አስተዳደር የዋንጫ ባለቤት ሆነዋል።
በተደረገው ስፖርታዊ ወድድር 4 ዋንጫዎችን በማንሳት የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር አጠቃላይ ውድድር አሸናፊ መሆን ችሏል።
በማጠቃለያው የዞን እና የወረዳ ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች የየወረዳዎቹ የስፖርት ልዑካን እና የስፖርት ቤተሰብ በተገኙበት ፍጻሜውን አግኝቷል።
ዘጋቢ: ሄኖስ ካሳ – ከሆሳዕና ጣቢያችን

More Stories
አርባምንጭ ዩኒቨርስቲ ሳውላ ካምፓስ ለ9ኛ ጊዜ በተለያዩ የሙያ መስኮች ያሰለጠናቸውን 121 ተማሪዎችን አስመረቀ
ዲግሪው “ወረቀት ብቻ ሳይሆን፣ የሀገር ተስፋና የትውልድ ኃላፊነት ነው” – አፈወርቅ ካሱ (ፕ/ር)
በክልሉ የተጀመሩ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ የድጋፍና ክትትል ስራ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የመጠጥ ውሃና ሳኒቴሽን ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ዶ/ር አስፋው ዲንጋሞ ገለጹ