ለችግር የተጋለጡ የህብረተሰብ ክፍሎችን ለመደገፍ የሚደረገው ጥረት ሊጠናከር እንደምገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የፋይናንስ ቢሮ አሳሰበ

ለችግር የተጋለጡ የህብረተሰብ ክፍሎችን ለመደገፍ የሚደረገው ጥረት ሊጠናከር እንደምገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የፋይናንስ ቢሮ አሳሰበ

ሀዋሳ፡ ጥር 29/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) ለችግር የተጋለጡ የህብረተሰብ ክፍሎችን ለመደገፍ የሚደረገው ጥረት ሊጠናከር እንደምገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የፋይናንስ ቢሮ ሀላፊ አቶ ተፈሪ አባቴ አሳስበዋል፡፡

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሠራተኛ እና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ በገቢ ማስገኛ ፕሮጀክቶች አፈጻጸም እና ቀጣይ ዕቅድ ዙሪያ ከባለ ድርሻ አካላት ጋር በአርባ ምንጭ ከተማ የምክክር መድረክ አካሂዷል።

ቢሮው በ2016 ዓ.ም በክልሉ በ13 ዞኖች ለሚገኙ ተጋላጭ የህብረተሰብ ክፍሎች 2 ነጥብ 8 ሚሊዮን ብር በመመደብ ከኢኮኖሚያዊ ችግር ለማላቀቅ በትኩረት መሥራቱን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሠራተኛ እና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ሀላፊ ዶ/ር ዋኖ ዋሉሌ ተናግረዋል።

በቀጣይም በክልሉ ባሉ ስድስት ከተሞች ለተጋላጭ የህብረተሰብ ክፍሎችን በመለየት በተለያዩ የሥራ ዘርፎች ለማሰማራት እና የገቢ ምንጭ እንዲፈጥሩ 5 ነጥብ 6 ሚሊዮን ብር መመደቡን ዶ/ር ዋኖ ገልጸዋል።

የክልሉ ፋይናንስ እና ኢኮኖሚ ልማት ቢሮ ሀላፊ አቶ ተፈሪ አባቴ እንዳሉት፤ በተለያዩ የኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ችግሮች የተጋለጡ የህብረተሰብ ክፍሎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በመምጣቱ መንግሥት በተለያዩ የገቢ ማስገኛ ዘርፎች ላይ በማሳተፍ ከችግር እንዲላቀቁ እየሠራ ነው፡፡

አክለውም ኃላፊው የተመደበው ሐብት ለታለመለት ዓላማ እንዲውል በትኩረት ሊመራ እንደሚገባ አሳስበዋል።

በመድረኩ ከክልሉ ከተለያዩ ዞኖች የተወጣጡ የሥራ ሀላፊዎች እና ባለድርሻ አካላት ተሳታፊ ሆነዋል።

ዘጋቢ፡ ወ/ገብርኤል ላቀው – ከአርባምንጭ ጣቢያችን