የገጠር ኮሪደር የአርሶና አርብቶ አደሩን የአኗኗር ዘይቤ በመቀየር መንደሮች ጽዱና ለኑሮ የተመቹ እንዲሆኑ ከማስቻሉም ባለፈ የአርሶአደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ፈይዳው የጎላ መሆኑ ተገለፀ

የገጠር ኮሪደር የአርሶና አርብቶ አደሩን የአኗኗር ዘይቤ በመቀየር መንደሮች ጽዱና ለኑሮ የተመቹ እንዲሆኑ ከማስቻሉም ባለፈ የአርሶአደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ፈይዳው የጎላ መሆኑ ተገለፀ

በሀገር አቀፍ ደረጃ የተጀመረው የገጠር የኮሪደር ልማት በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በስልጤ ዞን በአልቾ ውሪሮ ወረዳ ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል።

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት የተጀመረው የገጠር ኮሪደር ልማት የአርሶ አደሩን የአኗኗር ዘይቤ በመቀየር ጽዱና ጤናማ አካባቢ በመፍጠር መንደሮች ለኑሮ ምቹና ማራኪ እንዲሆኑ ከማስቻሉም ባለፈ የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ፋይዳው የጎላ መሆኑን የገለፁት የአልቾ ውሪሮ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ሱልጣን በርጋ ናቸዉ።

በገጠር ኮሪደር ልማት የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ በወረዳው በሚገኙ በሁሉም ቀበሌያት በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በዶሮ እርባታ፣ በንብ ማነብ፣ በወተትና በእንስሳት መኖ፣ በእንሰት ልማት አንዲሁም ለአካባቢ ጥበቃ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

የገጠር ኮሪደር ልማት በወረዳው ቀደም ባሉት ጊዜያት የተጀመረና አርሶአደሮች ሰፋፊ አውራ ጎዳናዎችን በባህላዊ መንገድ የማዘጋጀት፣ ዘመናዊ ቤቶችን የመገንባትና የማጠር፣ የሰዉና የእንስሳት መኖሪያ የመለየት ተግባር ከጥንት ጀምሮ ተግባራዊ እየተደረገ የመጣ የአርሶአደሩ የዘመናዊነት እሳቤ ማሳያ መሆኑን የገለፁት ምክትል አስተዳዳሪው፤ የገጠር ኮሪደሩን ከተቀናጃ የተፋሰስ ልማት ስራ ጋር በማቀናጀት መስራት እንደሚገባ አመላክተዋል።

በከተሞች የተለመደውን የአኗኗር ስርዓት ወደአካባቢያቸው በማምጣትና ባህላዊ ይዘቱን በመጠበቅ በመኖሪያ ቤት ግንባታ፣ የቤት አያያዝ እንዲሁም የአካባቢያቸውን ፅዳትና ውበት በመጠበቅ ዘመናዊ የአኗኗር ዘይቤ እየተከተሉ መሆኑንም የአካባቢው አርሶአደሮች ተናግረዋል።

የአካባቢያቸውን ጽዳት እና ውበት ከመጠበቅ በተጨማሪ በጓሮ አትክልትና ፍራፍሬ፣ በዶሮ እርባታ፣ በወተት፣ በእንሰት ብዜት፣ በእንስሳት መኖ የግብርና ስራዎችን በመስራት የምግብ ዋስትናቸውን ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያ በማቅረብ ተጠቀሚ መሆናቸውን አርሶ አደሮቹ አክለው ገልፀዋል።

ዘጋቢ: ሙጅብ ጁሃር – ከሆሳዕና ጣቢያችን