የተጎዳ መሬትን መልሶ ለማልማት የነቃ ተሳትፎ በማድረግ የበኩላቸውን እየተወጡ መሆናቸውን በጌዴኦ ዞን የይርጋጨፌ ወረዳ አርሶአደሮች ተናገሩ
ባህር ዛፍ የመሬትን ለምነት እየቀነሰ በመሆኑ ተክሉን በተፋሰስ ልማት ሥራ ከአርሶአደሩ ማሳ በዘመቻ የማስወገድ ተግባር መጀመሩን የወረዳው ግብርና ልማት ጽ/ቤት አስታውቋል፡፡
በጎርፍና በሌሎች ምክንያቶች የተጎዱ መሬቶችን መልሶ በማልማት የተገኙ ውጤቶችን በማየት የተፋሰስ ልማት ሥራ ተግባር በማሳቸው መጀመራቸውን የወረዳው አርሶ አደሮች ዓለሙ ጅግሶና በቀለ በየነ ገልፀዋል፡፡
ለአንድ ወር ቆይታ በዘመቻ በሚካሄደው በተፋሰስ ሥራ የተጎዳ መሬትን መልሶ ለማልማት የነቃ ተሳትፎ በማድረግ የበኩላቸውን እንደሚወጡ አርሶአደሮቹ ተናግረዋል፡፡
በወረዳው ዱመርሶ ቀበሌ ግብርና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ተሻለ ከፍያለው እንደገለፁት፤ በቀበሌያቸው በአንዳንድ አካባቢዎች በባህር ዛፍ ተክል የተሸፈኑ መሬቶች በአቅራቢያቸው በሚገኙ ሰብሎች ምርታማነት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እየፈጠረ ይገኛል፡፡
ችግሩን ለመቅረፍ ለአርሶአደሩ ግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት በመስጠት በዘመቻ ባህር ዛፍን በመንቀል በቦታው አርሶአደሩ ቡናና እንሰት እንዲተክል በማቀድ የእርሻ ቅድመ ዝግጅት መጀመራቸውን አቶ ተሻለ አስረድተዋል፡፡
የይርጋጨፌ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና ልማት ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ክፍሌ ጅግሶ እንደገለፁት፤ በተለያዩ ምክንያቶች የተጎዱ መሬቶችን ለይቶ በማቀድ የ2017 ዓ.ም የተፋሰስ ልማት ሥራ ጥር 15 በዘመቻ ተጀምሯል፡፡
የአፈርና ዉሃ ጥበቃ ሥራ፣ የቡና ጉድጓድ ዝግጅት፣ የተፈጥሮ ማዳበሪያ (የኮምፖስት) ዝግጅት፣ ተዳፋታማ የእርሻ ቦታዎችን እርከን የማዘጋጀት ሥራ በተፋሰስ ልማት ከሚከናወኑት ተግባራት የሚጠቀስ መሆኑን የተናገሩት አቶ ክፍሌ፤ የባህር ዛፉ የመሬትን ለምነት ስለሚቀንስ ተክሉን አርሶአደሩ ከማሳው እንዲያስወግድ በዘመቻ እየተሠራ ነው ብለዋል፡፡
ዘጋቢ፡ ውብሸት ኃ/ማርያም – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
የአፍላ ወጣቶችና ወጣቶችን የስነ ተዋልዶ ጤና ችግሮች ለመቅረፍ የተጀመሩ ጥረቶችን ለማጎልበት የጤና አደረጃጀቶችን ሚና ማሳደግ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ አስታወቀ
ወደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የመግባት ዕድል ያገኙ ተማሪዎች የበለጠ ውጤታማ ለመሆን ትምህርታቸው ላይ ብቻ ሊያተኩሩ እንደሚገባ መልዕክት ተላለፈ
የሀዲያ ዞን ፋይናንስ መምሪያ ለ2018 በጀት ዓመት ከ10 ቢልዮን ብር በላይ በጀት ለተለያዩ የልማት ስራዎች እንዲውል በተገቢው እንደሚሠራ ገለፀ